Ethiopia - Collective Agreements Database



በማሀቪር ኢንዱስትሪ ኃ/ተ/የግል ማኅበር

እና

በማሀቪር ኢንዱስትሪ ኃ/የተ/የግል ማኅበር

መሠረታዊ የሠራተኛ መኅበር



መካከል

የተደረገ የሕብረት ሥምምነት





 


መግቢያ 

የማሀቪር ጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካ ከተቋቋመ ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ የሕብረት ሥምምነት ለአሠሪና ሠራተኛ ሊኖር ስለሚገባው ግንኙነት፣ ኃላፊነት፣ የሥነ-ሥርዓት አከባበርና እርምጃ አወሳሰድ፣ የደመወዝ ጭማሪ፣ የዕድገት አሠጣጥና የደረጃ ምደባ እንዲሁም የልዩ ልዩ ጥቅማ ጥቅም መጠን አወሳሰን ስለምርትና ዕድገት፣ ስለሠራተኛ ድርጅቱ ደህንነት በአጠቃላይ ስለ ሠራተኛው መብትና ግዴታዎችን በተመለከተ ያስከተለውን ችግር ግምት ውስጥ በማስገባት፣ በአሠሪና ሠራተኛ አዋጅ ጉዳይ 377/1996 ስለ ህብረት ስምምነት የተገለፀውን ተግባራዊ ማድረግ በማስፈለጉና በአዋጅ ያልተካተቱ ነገር ግን አዋጁ በሕብረት ሥምምነት ሊካተቱ ይገባቸዋል፡፡ የሚላቸውን የአሰሪና ሰራተኛን ግንኙነት በየመብቱና ግዴታዎች አንፃር ዘርዝሮ ማስቀመጡ ሠላማዊ የሥራ ሁኔታና ምርታማነት እንዲሁም የሠራተኛውን ህይወት ለመለወጥ የሚኖረውን ጠቀሜታ በመረዳት፣ 

አሠሪና ሠራተኛ የተነጣጠሉ አካላት ሳይሆኑ፣ ተዋህደውና ተቀናጅተው ለጋራ ህልውናቸው የሚሰሩና አንደኛው ለሌላው አስፈላጊ በመሆናቸው ሊዳኟቸውና ሊቆጣጠሯቸው የሚገባ የጋራ ስምምነት ላይ መድረስ ወሳኝነት ስላለው፣ ይህንንም ለአሰሪው አካላት እና ለሰራተኛው በደንብና በሥነ-ሥርዓት ተንትኖ ማሳወቅ ጠቀሜታው ጉልህ በመሆኑ ቀጥሎ ያለው ሕብረት ሥምምነት ተደርጓል፡፡ ስለዚህ እያንዳንዱ ሠራተኛ በዚህ ህብረት ሥምምነት ላይ የተዘረዘዘሩ ግዴታዎችንና መብት ጠንቅቆ በመረዳት መብቱን ማስከብርና በዚያው መጠን ደግሞ ግዴታውን ለመወጣት ፋብሪካው ከሌሎች አምራች ፋብሪካዎች ጋር ተወዳድሮ የበለጠ አምራችና አሸናፊ ሆኖ በመገኘት ሠራተኛው ዕድገት ማምጣት እንዲችል፣ ለምርት ትኩረት እንዲሠጥ ይጠበቅበታል፡፡ በአሠሪውም በኩልም የሠራተኛውን መብት በስምምነቱ መሠረት መጠበቅና ለሥራና ለምርታማነት የሚያነቃቁ እርምጃዎችን በመወሰድ አስፈላጊ ያልሆኑ ጫናዎችን በማስወገድ የሠራተኛውን ጥያቄ በአግባብና ባልተንዛዛ ዲሞክራሲያዊ አሠራር እንዲሚያሟላ ይታመናል፡፡ 

ይህ የሕብረት ሥምምነት በሥራ ላይ በሚውልበት ጊዜ የሚከሰቱ ችግሮችን ለመፍታት የጋራ ጥረት ማድረግ የአንደኛው ወገን ግዴታ ብቻ አድርጎ ባለማየት ሁለቱም ወገኖች ለኢንዱስትሪ ሠላም መስፈንና ለጋራ ብልፅግና በመተባበር፣ በመተጋገዝና ሀሳብ ለሀሳብ በመለዋወጥ ተባብሮ የመስራት ባሕልን በማዳበር ረገድ ብዙ አስተዋፆ ይጠብቅብናል፡፡ ለወደፊቱ እንደአስፈላጊነቱ ለሕብረት ስምምነቱ መሻሻል መታረምና መበልፀግ ከሚያጋጥሙ ችግሮችና ልምዶች በመነሳት የየበኩላቸውን ጥረት ያደርጋሉ፡፡ 

ክፍል አንድ

አጠቃላይ ሥምምነት

አንቀጽ 1

የሕብረት ሥምምነት ዓላማ

  1. የሕብረት ሥምምነቱ ዓላማ በፋብሪካውና በሠራተኛው የጋራ ፍላጎት ላይ የተመሠረተ ሆኖ ዝርዝሩ እንደሚከተለው ይሆናል፡፡ 
  1. የሕብረት ሥምምነቱ በፋብሪካውና በሠራተኛው መካከል ሕጋዊ መሆኑ ታውቆ እንዲሠራ፡፡ 
  2. የፋብሪካውና የሠራተኛው አቋም ከሌሎች ከሚመሳሰሉ ፋብሪካዎች ጋር ተወዳዳሪ እንዲሆን፡፡ 
  3. የፋብሪካው የሥራ ዕቅድ ግቡን እንዲመታ በተቻለ ጥረት ማድረግና ምርቱ ጥራት እንዲኖረው ማድረግ፡፡   
  4. የዲሲፕሊንና የቅሬታ አቀራረብ ሥነ-ሥርዓት የሚመለከቱ ደንቦችን ለማውጣት፡፡ 
  5. በፋብሪካው ውስጥ ያለው የሰው ኃይል በሚገባ በሥራ ላይ እንዲውል ለማድረግ፡፡ 
  6. የሠራተኞቹን ጤንነትና ደህንነት መጠበቂያ ዘዴዎችና የመጠበቂያ መሣሪያዎች የሚሻሻሉበትን መንገድ መሻት፡፡ 
  7. ስለ ደመወዝ አከፋፈል ሥርዓትና ስነ ሥራ ሁኔታዎች አጠባበቅ ደንብ ማውጣት፡፡ 
  8. የፋብሪካውን አቋምና ንብረትን መጠበቅ፡፡ 
  9. ለፋብሪካው ሠራተኞች የሚያስፈልጉትን ልዩ ልዩ አገልግሎቶች የሚደራጁበትን ሁኔታ ማመቻቸት፡፡ 
  10. የፋብሪካው የሥራ ዘዴዎች እያሻሻሉና ዘመናዊ አቋም እንዲኖራቸው ለማድረግ፣ 
  11. የፋብሪካው ማኔጅመንትና የሠራተኛ ማኀበር ስለ ፋብሪካው እንቅስቃሴና ስለሠራተኞቹ እንደአስፈላጊነቱ ተገናኝተው በጋራ መወያየት፡፡ 
  12. ሠራተኛው ለሀገሩ እድገትና ልማት ድርሻውን ለማበርከት እንዲችል ፋብሪካው የተወሰነለትን የምርት ዕቅድ ግቡን እንዲመታና ለእያንዳንዱ ሠራተኛ ስራውን በጥራትና በቅልጥፋና እንዲሠራ ለማድረግ 
  13. ሥራ መናቅ፣ ሥራ ጠልነት፣ ሥነ-ሥርዓት አለማክበርን፣ ልግመኝነት ስንፍና፣ ንዝህላልነትን እና ብኩንነትና ካለፈቃድ ከሥራ መቅረት ሥርዓቶችን ወ.ዘ.ተ የመሣሠሉት ኋላ ቀርነትና ጎታች ባሕሎችና ልምዶች ጨርሶ ለማጥፋትና ሠራተኛው የበለጠ የሥራ ክቡርነት ገሚገባ ተገንዝቦ በላብ አደራዊ ዳሲፒሊን እንዲሠራ ለማድረግ፡፡ 
  14. የሠራተኞችን የኢኮኖሚና የማኅበራ ደህንነት ለመጠበቅና እንዲሁም ከጊዜ ወደ ጊዜ ሙያቸውንና ዕውቀታቸውን ለማሻሻልና በማኅበራዊና አስተዳደር ተሣትፎና ብቃት እንዲኖራቸው ለማድረግ፡፡
  15. ሠራተኛው መብትና ግዴታውን ጠንቅቆ እንዲያውቅ ትምሕርት ለመሥጠት፡፡ 
  16. ሠራተኛውን የሚመለከቱ ሕጎች የሕብረት ሥምምነት የአስተዳደር ደንቦች በሥራ ለማዋል፡፡
  17. ሠራተኛ የፋብሪካው ጥቅምና የሱ ጥቅም የተሳሰረ መሆኑን ለመረዳት የምርት መገልገያዎችንና ማንኛውንም የፋብሪካውን ንብረት በጥንቃቄ እንዲጠብቅ ለማድረግ፡፡ 
  18. የደመወዝ ጭማሪንና ሌሎች የገንዘብ ነክ ጥቅሞችን መወሰን
  19. የፋብሪካው ሠራተኞች በላብአደራዊ ዲሲፕሊን ታንፀው በአነስተኛ ወጪ ከፍተኛ የምርት ውጤት ለማስገኘትና የሠራተኞችን የነፍስ ወከፍ ምርታማነትን ከፍ ለማድረግና በአግባ የምርት ውጤት ቀጥተኛ ተጠቃሚ እርሱ መሆኑን ለማረጋገጥ፡፡ 
  20. ለፋብሪካችን ምርት በተግባር የሰለጠነ የሰው ኃይል ክምችትና ወሳኝ ከፍተኛ ሚና ያለው በመሆኑ የሰው ኃይል በዕቅድ ለማሰልጠንና ለመስራት፡፡ 
  21. አሁን ባለው የአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ አዋጅ 377/1996 እና ወደ ፊት የሚወጡ አዋጆችንና መመሪያዎችና ደንቦች የሚጠቀሱ የሕብረት ሥምምነት ዓላማዎችን በሙሉ ለማሟላት፡፡ 
  22. የሕብረት ሥምምነት ፀንቶ የሚቆይበት ጊዜ ለመወሰን፡፡ 

አንቀጽ 2

የቃላት ትርጉም

በዚህ ሕብረት ሥምምነት ውስጥ የተጠቀሱት ቃላት የሚከተሉት ትርጉም ይኖራቸዋል፡፡ 

  1. “አዋጅ” ማለት የአሰሪና ሰራተኛ ጉዳይ አዋጅ 377/1996 ማለት ነው፡፡ 
  2. “ሠራተኛ” ማለት በአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ አዋጅ 377/1996 አንቀጽ 4 በሚያመለክተው መሠረት ከአሠሪ ጋር በቅጥር ላይ የተመሠረተ የሥራ ግንኙነት ያለው ግለሰብ ነው፡፡ 
  3. “ፋብሪካ” ወይንም “አሠሪ” ማለት የማሀቪር ጨርቃ ጨርቅ ማለት ነው፡፡ 
  4. “ማኅበር” ማለት የማሀቪር ጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካ ሠራተኞች ማኅበር ማለት ነው፡፡ 
  5. “ክፍት የሥራ ቦታ” ማለት ለፋብሪካው ዕድገትና መሥፋፋት አስፈላጊነቱ ተረጋግጦ በአሠሪው ፈቃድ የተከፈተ አዲስ የሥራ መደብ ወይንም ሠራተኛ ኖሮበት የተለቀቀና ተተኪ ሠራተኛ የሚያስፈልገው የሥራ መደብ ማለት ነው፡፡ 
  6. “ትርፍ ሠዓት” ማለት በአዋጅና በዚህ ሥምምነት ውስጥ በግልፅ ከተጠቀሱት የሥራ ሠዓቶች በላይ በአሠሪው ፈቃድ ሠራተኛው ከመደበኛ የሥራ ሰዓት ውጪ በትርፍ የሰራበት ጊዜ ነው፡፡ 
  7. “ዓ.ም” ማለት ለዚህ ሕብረት ስምምነት ወይም በመንግስት ህጎች መመሪያዎች በግልፅ ካልተሠጠ በቀር እንደ ኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር ከመስከረም እስከ ጳጉሜ 5 ወይም 6 ነው፡፡ 
  8. “ፈቃድ” ማለት የዓመት ዕረፍት፣ የሕመም፣ የሐዘን፣ የወሊድ፣ የጋብቻ፣ ማኅበር ሥራ ወዘተ… የፈቃድ ዓይነቶች ማለት ነው፡፡ 
  9. “የሥራ ልብስ” ማለት በዕቅድና በዚህ ሕብረት ስምምነት መሠረት የሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ኤክስፐርት አጥንቶ፣ ለእያንዳንዱ የሥራ ክፍል እንደ አስፈላጊነቱ ሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ በፅሁፍ ሲፈቅድ በተወሰነ ጊዜ ውስጥ ለሠራተኛ የሚሰጥ መከላከያ ነው፡፡ 
  10. “የአደጋ መከላከያ” ማለት በፋብሪካ የሥራ ሒደት የተነሳ በሠራተኛው ላይ ሲደርስ የሚችለውን ማንኛውም አደጋ ወይም ጉዳት ለመከላከል ያስችላል ተብሎ የሠ/ማ/ጉዳይ ሚኒስቴር ኤክስፐርት አጥንቶ ለእያንዳንዱ የሥራ ክፍል አስፈላጊ መሆኑን አምኖበት በፅሑፍ ሲፈቅድ ለሠራተኛው በተወሰነ ጊዜ የሚሰጥ መከላከያ ነው፡፡ 
  11. ዕድገት “ማለት ከዚህ በላይ በተራ ቁጥር 5 በተመለከተው ሁኔታ በተገኘው ክፍት የሥራ መደብ በዝቅተኛ የሥራ መደብ ላይ የነበረ ሠራተኛ ተወዳድሮበትና በአሰሪው ፀድቆ የሚሰጥ የእድገት ቦታ ነው፡፡”         
  12. “ዝውውር” ማለት በዚህ ሕብረት ሥምምነት መሠረት የፋብሪካው የአስተዳደር ሠራተኛው የተሻለ አገልግሎት ይሰጣል ብሎ ያመነበትን ከአንዱ የሥራ ክፍል ወደ ሌላ የሥራ ክፍል ወይም ከፈረቃ ወደ ፈረቃ እንዲሁም ከፋብሪካ ወደ ሌላ ፋብሪካ ማዛወር ነው፡፡ 
  13. “ማስጠንቀቂያ” ማለት ከቃል ማስጠንቀቂያ ጀምሮ በደረጃ ከ/ስራ ውል ማቋረጥ በፊት የሚሠጥ እስከ መጨረሻ የፅሁፍ ማስጠንቀቂያ ድረስ ያለው ሲሆን፣ በአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ አዋጅ 377/1996 አንቀጽ 28 የሚጠቃለል ነው፡፡ 
  14. “ጥቅማ ጥቅም” ማለት በዚህ ሕብረት ሥምምነት መሠረት ለሠራተኛው የሚሠጥ ጥቅም ነው፡፡ 
  15. “የሥራ ስንብት ክፍያ” ማለት በአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ አዋጅ 377/1996 አንቀጽ 39 መሠረት የሚፈፀም ክፍያ ነው፡፡ 
  16. “ደመወዝ” ማለት አንድ ሠራተኛ በሥራ ውሉ መሠረት ለሚያከናውነው ሥራ የሚከፈለው መደበኛ ክፍያ ማለት ነው፡፡ 
  17. “ትርፍ” ማለት በባጀት የተያዘ /በጀተሪ ፕሮፊት/ ሳይሆን ያለፈውን ዓመት ሒሳብ ዘግቶ የተገኘውን ከታክስ በኋላ ያለውን የተጣራ ትርፍ ነው፡፡ 
  18. “የሠራተኛ ነፍስ ወከፍ ውጤት /ምርታማነት/” ማለት የፋብሪካው ምርት ውጤት ዋጋ ሽያጭ ታክስን ሳይጨምር የሚገኘው ጠቅላላ የሥራ ሠዓቶችን መጠን በማካፈል የሚገኝ ውቴት ነው፡፡ 
  19. “ቤተሰብ” ማለት 

ሀ/ ሕጋዊ የሠራተኛው/ዋ/ ባል ወይም ሚስት 

ለ/ ዕድሜያቸው ከአስር ስምንት ዓመት በታች የሆኑ የሠራተኛው/ዋ ልጆች 

ሐ/ በሠራተኛው/ዋ ድጋፍ ይረዱ የነበሩ የሟች ወላጅ ቤተሰብ ነው፡፡ ወይም ቤተሰብ ማለት የሠራተኛ ሕጋዊ ሚስት ወይም ሕጋዊ ባል ዕድሜያቸው ከ18 ዓመት በታች የሆኑ እራሳቸውን ችለው የማይተዳደሩ የሠራተኛው/ዋ ልጆችና በሠራተኛው/ዋ ይረዱ የነበሩ ወላጆች ቤተሰብ ነው፡፡ 

  1. “ሕጎች” ወይንም “መመሪያዎች” ማለት የአሠሪና ሠራተኛን ግንኙነት በሚመለከት መንግስት ያወጣቸውንና ወደፊት የሚያወጣቸውን ሕጎች ወይንም መመሪያዎች ማለት ነው፡፡ 
  2. “የሥራ ክርክር” ማለት በአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ አዋጅ 377/1996 አንቀፅ 136 ቁጥር 3 መሠረት ሕግን፣ ሕብረት ሥምምነትን፣ የሥራ ደንብ፣ የሥራ ውልን ወይንም ሲሠራበት የቆየ ልምድን መሠረት በማድረግ እንዲሁም ከሕብረት ሥምምነት ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን በሚመለከት በሠራተኛ በአሠሪ ወይንም በሠራተኞች ማኅበርና በአሠሪዎች መካከል የሚነሣ ክርክር ነው፡፡ 
  3. “የሥራ መደብ” ማለት በፋብሪካው የሠው ኃይል መዋቅር መሠረት በፋብሪካው ውስጥ ያሉትን የሥራ መደቦች ማለት ነው፡፡ 




አንቀጽ 3

የሕብረት ሥምምነት አተረጓጎም

  1. በዚህ ሕብረት ሥምምነት ውስጥ የተዘረዘሩትን ሁኔታዎች ትርጉም በሥራ ላይ ለማዋል የአፈፃፀም ችግር ወይንም ያለመግባባት ቢፈጠር የአንቀፁ ወይንም የሁኔታው ትርጉም በአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ አዋጅ 377/1996 ወይም አግባብነት ባላቸው ሌሎች ሕጎች ተጠቅሞ መተርጎም ይቻላል፡፡

አንቀጽ 4

ስህተትን የማረም መብት

  1. በዚህ ሕብረት ሥምምነት ወይንም ሌሎች ሕጎችና መመሪያዎች ያልተፈቀዱ ሁኔታዎች በመፈፀማቸው እንዲታወቅ አሠሪና ሠራተኛ ማኅበሩ ተገቢውን ማሻሻያ ወይንም ማረሚያ ማድረግ የተፈቀደ ነው፡፡ 
  2. በተጠቃሚ ጥፋት ወይንም የተንኮል ሥራ ሳይሆን በስህተት ወይም በሌላ 3ተኛ ሰው ጥፋት ለሠራተኛው ያለአግባብ የተከፈለ ገንዘብ ሲኖር ፋብሪካው ወይም አሠሪው የሂሳቡን አከፋፈል ጊዜ ሊያራዝምለት ይችላል፡፡  
  3. ስህተት የተፈፀመው በተንኮል ወይም ሆን ተብሎ በተደረገ ማሳሳት ሲሆን አሰሪው በዚህ ሕብረት ስምምነት በተጠቀሱት እርምጃዎች ተመጣጣኝ እርምጃ በአጥፊው ላይ በመውሰድ ተፈላጊውን ሒሳብ ማስከፈል ይችላል፡፡ 
  4. ስለሆነም ሠራተኛው ያለውን ጥቅምና መብት በአዋጅ ስለይርጋ የተመለከተውን ጊዜ ከማለፉ በፊት መጠየቅ አለበት፡፡ 

አንቀጽ 5

ተጨማሪ ሥምምነቶችን ስለማድረግ

  1. ፋብሪካው ወይም አሰሪው የየክፍሉ ኃላፊዎች የየዕለቱን ተግባርና መሠረታዊ ዓላማዎች ምርቱንና ሠራተኛውን ማስተባበርና ማስተዳደር የታለመለትን ውጤት እንዲያስገኝ ተገቢውን ጥረት ማድረግ ሲሆን፣ መሣሪያውና ሠራተኛም የማይነጣጠሉ የምርት ኃይሎች እንደመሆናቸው መጠን ልዩ ጥንቃቄና እንክብካቤ ይደረግላቸዋል፡፡ 
  2. ይህንንም መሠረታዊ ዓላማ ከግቡ ለማድረስ ለፋብሪጃካውና ለሠራተኛው አስፈላጊ የሆኑ ሕጋዊ ሁኔታዎችን ለማሟላት አሠሪውና ማኅበሩ አስፈላጊ በሆኑ ወቅቶች እየተገናኙ በመወያየት ለመንደፍ የሚያስችሉ ሀሳቦችን ሊለዋወጡ ይችላሉ፡፡ 
  1. አሠሪውና የሠራተኛ ማኅበሩ ለፋብሪካው የሥራ እንቅስቃሴ፣ ስለ ሠራተኞች ሁኔታና ስለተለያዩ ችግሮች በየሦስት ወሩ ተገናኝተው በመወያየት መፍትሔ ይሻሉ፡፡   
  2. እስከ ተወሰነው የስብሰባ ጊዜ ድረስ ለመቆየት የማያስችል አስቸኳይ ጉዳይ ሲያጋም የሠ/ማኅበሩ ሊቀመንበርና የፋብሪካው ሥራ አስኪያጅ ይነጋገሩበታል፡፡ ሆኖም በጣም አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ የሠ/ማኅበሩ ሊቀመንበር ከሠ/ማኅበሩ የስራ አሥፈፃሚ ኮሚቴ አባላት ጋር በመሆን እና የፋብሪካው ሥራ አስኪያጅ የሚመለከታቸውን የመምሪያና አገልግሎት ኃላፊዎች ጋር በመሆን ይነጋገሩበታል፡፡ 
  1. አሰሪና የሰራተኛ ማህበር ወደፊት አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ በዚህ ህብረት ሥምምነት ያልተጠቀሰ ተጨማሪ ስምምነቶች ሊያደርጉ ይችላሉ፡፡ 
  2. መንግስት በሀገሪቱ ተጨባጭ ሁኔታ ላይ ተመርኩዞ ከሚያወጣቸው ሕጎች ደንቦችና መመሪያዎች ለሠራተኛው የሚፈቅዱለት ሁኔታዎችን በተቻለ መጠን ከዚህ ሕብረት ሥምምነት ጋር ተስማምተው ተግባራዊ እንዲሆኑ አስፈላጊውን ዝግጅት በየወቅቱ ያደርጋሉ፡፡ 
  3. ከዚህ በላይ በተገለፁት ሁኔታዎች ምክንያት የሚደርስባቸው ሥምምነቶች ለሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ቀርበው ይመዘገባሉ፡፡ 

አንቀጽ 6

የጋራ መብትን ስለማወቅ

  1. የአሠሪውን መብት ስለማወቅ 
  1. በዚህ የሕብረት ሥምምነት በተለይ የተወሰነ ካልሆነ በስተቀር ፋብሪካው ሠራተኛን እንደየደረጃው ለመመደብ፣ የስራ ፕሮግራም ለማውጣት፣ አዲስ የስራ ዕቅድ ለማዘጋጀት፣ የሥራ ትዕዛዝ ለመሥራት፣ የምርት ጥራትና ብዛት ለመቆጣጥር፣ አዲስ ሠራተኛ ለመቅጠር፣ ለተቀጠሩትም ሠራተኞች ዕድገት ለመሥጠት፣ ሠራተኛን ለማዛወር፣ የሥነ-ሥርዓት እርምጃ ለመውሰድ፣ በዚህ ሕብረት ሥምምነትና በአሠሪና ሠራተኛ ጉይ አዋጅ 377/1996 መሠረት ለማሰናበት፡፡ 
  2. የአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ አዋጅ 377/1996 ይህ ሕብረት ስምምነት እና የመንግስት አዋጆች በትክክልነና በሚገባ ስራ ላይ መዋላቸውን የመከታተል መብት አለው፡፡ 
  1. የሠራተኛ ማኅበሩን መብት ስለማወቅ 
  1. አሠሪው የሥራ ሁኔታዎችን፣ የሥራ ክርክር፣ የህብረት ስምምነት የሚመለከቱ ተመሳሳይ ጉዳዮች ማኅበሩን ሕጋዊ አድራጎት ይቀበላል፡፡ 
  2. የሠራተኛ ማኅበሩ ከዚህ በላይ በን/ቁ 1.2 በተመለከተው መሠረት ሠራተኛውን መወከልና ሠራተኛውም ሕግና የሕብረት ሥምምነት በሚፈቅደው መሠረት በፋብሪካው የሥራ ዕቅድ አፈፃፀምና አስተዳደር ተሳትፎ እንዲኖረው አስፈላጊውን ጥረት ሁሉ ያደርጋል፡፡ 
  3. በየክፍሉ የሚመረጡ የማኅበሩ ተጠሪዎች ዋና ተግባር ሥራና ሠራተኛን በተስተካከለ ሁኔታ ማስተባበር ስለሆነ በዚህ ሕብረት ሥምምነት አንቀጽ 10 የተዘረዘረውን መብት ፋብሪካው ወይም አሰሪው በሚገባ ያውቅላቸዋል፡፡ 

ክፍል ሁለት

መብቶችና ግዴታዎች

አንቀጽ 7

የፋብሪካው ወይም የአሠሪ መብቶች

  1. በዚህ ሕብረት ሥምምነት ወይም በአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ አዋጅ 377/1996 በግልፅ ካልተመለከተ በስተቀር ማንኛውም የፋብሪካ ሥራ ለማቀድ፣ ለመሥራት፣ ለመቆጣጠር፣ ሠራተኛን በአስፈላጊ ቦታ ለመመደብና ዕድገት ለመስጠት፣ በቂ በሆነ ምክንየት ከቦታ ቦታ ለማዛወር፣ 
  2. በአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ አዋጅ 377/1996 እና በዚህ ሕብረት ሥምምነት መሠረት በበቂ ምክንያት ለመቅጣት፣ ከደረጃ ዝቅ ለማድረግ፣ ከሥራ ለማገድ፣ ከሥራ ለማሠናበት ወይም ለ45 ቀናት አግዶ ለማቆየት፣ 
  3. አዲስ የሥራ ቦታ መከፈት ለነበረው የሥራ ቦታ የሠራተኛ አስፈላጊነቱን ለመወሰን፣ የሥራ መደብ አስፈላጊውን የሠራተኛ ኃይል መመጠን፣ ለሥራዎቹ የሚያስፈልጉትን የት/ደረጃና የስራ ልምድ ለመወሰን፣ አዲስ ሠራተኛ በሕጉ መሠረት ለመቅጠር፣ ተወዳድሮ ላሸነፈ ሠራተኛ በዚህ የሕብረት ሥምምነት መሠረት ለመቅጠር፣ የደረጃ ዕድገት ለመሥጠት፣ ሊወሰድ ለሚገባው የሥነ-ሥርዓት እርምጃዎች ለማሻሻል ወይም ይቅርታ ለማድረግ፣ 
  4. ስለ ፋብሪካው የሥራ ሁኔታዎች፣ ስለ ፋብሪካው ሀብትና ንብረት አጠባበቅ ከሌላ ሶስተኛ ወገን ጋር ለመነጋገር፣ ስለ ዕቃ ግዢና ሽያጭ ለመዋዋል፣ ኢንሹራንስ ለመግባት አስፈላጊ የሆነ ሌላም ውል ለመዋዋል፡፡ 
  5. በሌላ አኳኋን ካልተገለፀ በስተቀር ፋብሪካውን የስራና ሠራተኞችን በሚመለከቱ ጉዳቶች መግለጫ መስጠትና ማስታወቂያ ለማውጣት የት/ት ፕሮግራም የማውጣት መብት የፋብሪካው ነው፡፡ 
  6. ከሠራተኛ የሚፈለጉ የፋብሪካ ብድሮችነን ሠራተኛው ከፋብሪካው ጋር በሚያደርጋቸው ስምምነቶች መሠረት በሕጋዊ ባለመብቶች ለማስተላለፍ የመሳሰሉት ተግባሮች ለማከናወን መብት አለው፡፡ 
  7. አሠሪው ወደ ፋብሪካ ቅጥር ግቢ ሲገቡና ሲወጡ ማንኛውንም ሰውና ተሽከርካሪ መፈተሽ ይችላል፡፡ 
  8. ፋብሪካው አስፈላጊ ሆኖ ሲያገኘው ለማህበሩ በማሳወቅ ሽፍት ለማጠፍ ይችላል፡፡ 

አንቀጽ 8

የፋብሪካው ግዴታዎች

  1. በአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ አዋጅ 377/1996 ወይም በሌሎች የመንግስት ሕጎችና መመሪያዎች ወይም በዚህ ሕብረት ሥምምነት ውስጥ የሠፈሩትን መብትና ግዴታዎች በትክክል ሥራ ላይ መዋል፡፡ 
  2. ማንኛውም የፋብሪካው ሠራተኛን ደመወዝ በሚቀበልበት ወቅት ከደመወዙ ላይ ተቀናሽ የሆኑትን በዝርዝር የሚያስረዳ ፎርም /ቢል/ ከደመወዙ ጋር ወይም ደመወዙን ለመቀበሉ በፊት መስጠት አለበት፡፡ ይህንንም የሒሳብ ክፍሉ ሥራውን በሚያመች መንገድ ይፈፅማል፡፡ የሰራተኛው ደመወዝ ወር በገባ በ28ኛው ቀን መክፈል ይገባዋል፡፡ ቀኑ በዓል ወይንም እሁድ ከሆነ ከዚሁ ቀን አስቀድሞ ባለው የሥራ ቀን ይከፍላል፡፡ 
  3. ፋብሪካው ጠቅላላ ሠራተኞችን በሚመለከት ነገር ሁሉ ማናቸውም የሥራ መመሪያ ለውጦች የሚያደርግበት የሥራ ጊዜ በቅድሚያ ማኅበሩ እንዲያውቀው ያደርጋል፡፡ ሆኖም ማኅበሩ ለውጡ በሠራተኞች ላይ ጉት የሚያደርሱ መስሎ ከታየው ከፋብሪካው ጋር ይነጋገርበታል፡፡ ይህም ለውጥ በዚህ ሕብረት ሥምምነት የተፃፉትን ጉዳዮች የሚሽር ወይም የሚቃረን መሆን የለበትም፡፡ 
  4. ማንኛውም ሰራተኛ የሰራተኛ ማህበር አባል እንዲሆን ወይም እንዳይሆን ወይም አባልነቱን እንዲተው ለማድረግ ሰራተኛ መካከል ልዩነት አያደርግም፡፡ 
  5. ፋብሪካው በብሔረሰብ ወይም በፆታ፣ በሐይማኖት፣ በፖለቲካ አመለካከት ምክንያት በሠራተኛ መካከል ልዩነት አያደርግም፡፡ 
  6. የሰራተኛው ማህበር አባል የሆኑትን እንዲሁም የሰራተኛ ማህበር አባል ያልሆኑትን ከሆኑት በማማረጥ ምንም አይነት አድሎ አያደርግም ወይም የሰራተኛውና ማህበር መሪ በመሆናቸው የዕድገት ደረጃቸውን አይነፍግም፡፡ 
  7. የአንድን ሠራተኛ በመንግሥት አዋጆች፣ መመሪያዎችና ደንቦች፣ በዚህ ሕብረት ሥምምነት የተሠጠውን ሕጋዊ መብት በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መልክ እንዲቀንስ አያደርግም፣ ክብሩን የሚነካ ሕገ-ወጥ ተግባር አይፈፅምበትም፡፡ 
  8. ለሥራ አስፈላጊ የሆኑትን ቢሮዎች፣ ሥራ መሣሪያዎችና ለሥራው የሚያስፈልጉ ጥሬ ዕቃዎችን በተሟላ ሁኔታ ለሠራተኞች ያቀርባል፡፡ 
  9. ፋብሪካው በብዛትም ሆነ በሙሉ ሠራተኞችን ከአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ አዋጅ 377/1996 ውጪ አይቀንስም፣ ይኸውም ሲሆን ፋብሪካው ይህንን እርምጃ ከመውሰዱ በፊት ለማሕበሩ በቅድሚያ ያሳውቃል፡፡ 
  10. ፋብሪካው ማንኛውንም ሠራተኛ ሲቀጥርም ሆነ ዕድገት ሲሰጥ፣ ከቦታ ቦታ ሲያዘዋውር ለሠራተኛው በፅሁፍ ይሠጠዋል፡፡ ይህንንም ለሚመለከታቸው የሥራ መምሪያዎች ሁሉ በፅሁፍ ያሳውቃል፡፡ 
  11. በሥራ ምክንያት ለሚደርሱ አደጋዎች /በሽታዎች/ በአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ አዋጅ 377/1996 መሠረት በሠራተኛ በሥራ ላይ ለሚደርሱ አደጋዎች እንዲሁም በሥራ ምክንያት ለሚመጡ በሽታዎች አሠሪው /ፋብሪካው/ ኃላፊ ይሆናል፡፡    
  12. በፋብሪካው ጊቢ ውስጥ ለሠራተኛው አገልግሎት የሚውል የሕዝብ ስልክ እንዲገባ ፋብሪካው ለሚመለከተው የመንግስት አካል ጥያቄውን አቅርቦ እንዲፈፀም ጥረት ያደርጋል፡፡ 
  13. የፋብሪካው የእሳት አደጋ መከላከያ የተሟላ ሆኖ ለዚህ ሥራ በቂ ችሎታ ያላቸውን ሠራተኞች በሙሉ ትጥቅ ጋር እንደ አስፈላጊነቱ ያቀርባሉ፡፡ 
  14. የጥበቃ ሠራተኞች ተግባራቸውን በትክክል ሥራ ላይ ለማዋል እንዲችሉ ፋብሪካው አስፈላጊውን የጥበቃ መሣሪያ ያቀርባል፡፡ ሥራውን በሚመለከት አስፈላጊውን ትምህርት እንዲሰጣቸው ያደርጋል፡፡ 
  15. ፋብሪካው ለሠራተኞች በላስቲክ ወይም በማይካ የተሸፈነ የሠራተኛ ፎቶ ግራፍ ያለበት የሚሠራበትን ቦታ ጨምሮ የሚያመለክት ሆኖ ተዘጋጀ የመታወቂያ ካርድ ያዘጋጃል፡፡ ከአረጀ አሮጌውን አስረክቦ ይለወጥለታል፡፡ ከጠፋበት ግን በፖሊስ አስመስክሮ ማስረጃ ካመጣ ዋጋውን ከፍሎ ምትክ ይሠጠዋል፡፡ 
  16. ለፋብሪካውና ለሥራው ደህንነት ጎጂ የሆኑትን ጠንቆች ለማስወገድ ወይም ለማሻሻል በባለሙያ አስጠንቶ አስፈላጊውን ማሻሻያ ያደርጋል፡፡ 
  17. ፋብሪካው ለሠራተኞች አስፈላጊ በሆኑ ቦታዎች የመጠጥ ውሃና ገላ መታጠቢያና መፀዳጃ ያዘጋጃል፡፡ ለመሣሪያዎች እንደ አስፈላጊቱ በየጊዜው ጥገናና ክትትል ያደርጋል፡፡ 
  18. ቆሞ የነበረው ማሽን በመነሳቱ ወይም በድንገተኛ እሳት አደጋ ወይም አስፈላጊ በሆነ ጥሪ ወይም በሕመም በቀሪ የምርት መለዋወጥ ሁኔታ ሲያጋጥም ካልሆነ በቀር ሠራተኛው ከፈረቃ ቅያሪ አርባ /40/ ደቂቃ በኋላ ከቦታ ወደ ቦታ እንዲቀየር አያደርግም፡፡ ይህ ድንጋጌ ሪዘርቭ ሠራተኞችን አይመለከትም፡፡ 
  19. የአንድ ሠራተኛ የዕድገት ዕድሉን ለመግታት ወይም ሠራተኛውን ለመጉዳት ሲባል ከአንድ የሥራ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ አያዛውርም፡፡ 
  20. ፋብሪካ ውስጥ የሚሠሩ ቋሚ ሠራተኞች ሁሉ የወር ተከፋዮች እንዲሆኑ ያደርጋል፡፡ 
  21. የፋብሪካ ሠራተኞች ለሕክምና፣ ለሥራ፣ ለሥልጠና እና ከፋብሪካው በተገኘው ልዩ ልዩ ጉዳዮች ወደ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ሲላክ የሠራተኞችን ጉዳይ ተቀብሎ በአግባቡ ያስፈፅማል፡፡ 
  22. ሠራተኛው በሥራ ምክንየት በሚሄድባቸው ስፍራዎች በሚደርስበት አደጋና ሕመም አስፈላጊውን እርዳታ ሲጠይቅ ገንዘብ ትራንስፖርትና ልዩ ልዩ የሚያስፈልጉ እርዳታዎች ያደርጋል፡፡ 
  23. ሠራተኛው በሕመም ምክንያት የሕክምና ቦርድ በሚወስነው መሠረት በቅጥር ውሉ ላይ ከተመለከተው የተለየ ሥራ እየሰራ፣ ሠራተኛው ከደረሰበት መለስተኛ አደጋ ወይም በሽታ እንዲያገግም በጊዜያዊነት ሲያዝ ፋብሪካው የሰራተኛውን መብት ሳይቀንስ ወደ ሌላ አመቺ የሥራ ቦታ ይዛውረዋል፡፡ 
  24. ፋብሪካው ከፋብሪካው ክሊኒክ አቅም በላይ ለሆነ ሕክምና በክሊኒኩ ትዕዛዝ መሰረት ወደ ሌላ ሆስፒታል ለሚላኩ ሠራተኞች ከተለያዩ ሆስፒታሎች ጋር የዱቤ ሕክምና ውል ይገባል፡፡ 
  25. ፋብሪካው የሙከራ ወይም የሥልጠና ጊዜውን ላጠናቀቀ ሠራተኛ ከሥራ መደቡ ላይ ለመመደቡ ከሚደርሰው ደብዳቤ ጋር የሥራ መደቡ ዝርዝር ተግባርና ኃላፊነት (ጆብ ዲስክሪፕሽን) ይሠጣል፡፡ 
  26. ፋብሪካው የሰዓት መቆጣጠሪያ ፓንች ያዘጋጃል፡፡ 
  27. ፋብሪካው ባለሙያ በሚወስነው መሠረት ለሠራተኞች ከድርጅቱ ውጪ የጤና ምርመራ ያደርጋል፡፡                                    

አንቀጽ 9 

የሠራተኛ ማኅበሩ መብቶች 

  1. ፋብሪካው የማኅበሩን ስለማንኛውም የሥራ ሁኔታዎች የሕብረት ክርክርና የሕብረት ስምምነት አንድ አካል አድርጎ ይቀበላል፡፡ 
  2. ፋብሪካው በማንኛውም የሠራተኛ ማኅበር አባል፣ በሠራተኛ ማኅበር የሥራ አስኪያጅ ኮሚቴ የሚሰጠውን ሕጋዊ ተግባር እንዲፈፅም ወይም እንዲያስፈፅም ሊከለክለው አይገባም፡፡ እንዲሁም ማኅበሩ በመሪነት የሚያገለግሉት ሰዎች ፋብሪካው ከዚህ ሥምምነት ውጪ የተለየ እርምጃ ሊወስድባቸው አይችልም፡፡ 
  3. የማኅበሩ ሥራ አስኪያጅ ኮሚቴ የማኅበሩን እንግዳ የፋብሪካውን አስተዳደር በቅድሚያ በፅሁፍ በማሳወቅ ወደ ፋብሪካው ይዞ ሊገባ ይችላል፡፡ 
  4. ፋብሪካው በየጊዜው አዲስ የሚቀጠሩ ወይም የሚሠናበቱ ሠራተኞች ሲኖሩ በቅድሚያ በግልባጭ ለማኅበሩ ያሳውቃል፡፡ 
  5. ማኅበሩ በየወሩ የሚጨመሩትንና የሚቀነሱትን ማኅበርተኞች ብዛትና ከማኅበርተኞች የተቆረጠውን ገንዘብ ልክ ማወቅ ይችላል፡፡ በአንዳንድ ምክንያት የአባልነት ክፍያ ያልከፈሉ ቢኖሩ ያልተቀነሰው ገንዘብ በሚቀጥለው ተቀንሶ ለማኅበሩ ገቢ ይሆናል፡፡ 
  6. ማኅበሩ በፋብሪካው ውጥያ ያሉትን የራሱ ሰሌዳዎች ለማስታወቂያ መለጠፊያ ይጠቀምባቸዋል፡፡ ማኅበሩ ማናቸውንም ማስታወቂያዎች በኃላፊነት ሊለጥፈው ይችላል፡፡ ሆኖም የሚለጠፈው ማስታወቂያ ግልባጭ ለፋብሪካው እንዲያውቀው ይሰጣል፡፡ 
  7. የፋብሪካው ሠራተኞች ልዩ ልዩ የሕብረት ሥራዎች ለማቋቋም በሚፈልጉበት ጊዜ እያንዳንዳቸው በፈቃደኝነት የፈረሙበት የስም ዝርዝርና የገንዘብ ልክ በማኅበሩ ደብዳቤ አማካኝነት ሲደርሰው ፋብሪካው የተባለውን ገንዘብ ከደመወዛቸው ላይ ቆርጦ ማኅበሩ ላዘዘበት ድርጅት ወይም ሰው ይከፍላል፡፡ 
  8. በዚህ አንቀጽ 3 ንዑስ ቁጥር 6 መሠረት በፋብሪካው አማካይነት የተቀነሰው መዋጮ ገንዘብ ፋብሪካው ለማኅበሩ ይከፍላል፡፡ ማኅበሩም ከአባሎቹ የተቀነሰው ገንዘብ ትክክለኛ መሆን አለመሆኑን የመቆጣጠር መብት የተጠበቀ ነው፡፡ 
  9. ማንኛውም ሠራተኛ በራሱ ፈቃድ ማኅበርተኘነቱን ለመልቀቅ ፈልጎ ለሠራተኛ ለማኅበሩ ሲያመለክት ወይም ማኅበሩ ሠራተኛውን ከማኅበሩ ሲያስወጣ ይህንኑ በፅሁፍ ማኅበሩ ለፋብሪካው ሲያሳውቅ ከማኅበርተኛው ላይ ይቆረጥ የነበረውን መዋጮ ገንዘብ መቆረጡ ይቆማል፡፡ 
  10. ማኅበሩ ለማኅበሩ ሥራ ጉዳይና ቅሬታ ከሚቀርቡለት እንዲሁም ስብሰባ ተሳትፎ በሚያደርጉበት ወቅት ማኅበሩ በፅሁፍ ሲጠይቅ አስፈላጊውን ትብብር ሁሉ የማገኘት መብት አለው፡፡ 
  11. በሕጉ መሠረት ለማኅበሩ ሥራ ከመደበኛ ሥራው ላይ እንዲነሳ የተደረገ የማኅበሩ ተመራጭ ያገኘ የነበረው ጥቅማ ጥቅም ይጠበቅበታል፡፡ 
  12. የማኅበሩ ሥራ አስፈፃሚዎች በወር አንድ ቀን የማኅበሩን ሥራ እንዲሠሩ ድርጅቱ ፈቃድ ይሠጣቸዋል፡፡ 
  13. ከማኅበሩ ሥራ አስፈፃሚዎች መካከል የማኅበሩ ሊቀመንበርና ዋና ፀኃፊ በወር ሁለት ቀን የማኅበሩን ሥራ እንዲሰሩ ድርጅቱ ፈቃድ ይሠጣል፣ 

አንቀጽ 10

የሠራተኛ ማኅበር ግዴታዎች

  1. የመንግስት ሕጎች ደንቦችና መመሪያዎችን እንዲሁም ላብአደራዊ ሥነ-ምግባር መከበሩና ይህ የሕብረት ሥምምነት በሠራተኛው ዘንድ ታውቆ በትክክል ተከብረው ሥራ ላይ መዋላቸውን ማረጋገጥ፡፡ 
  2. የሥራ ሰዓት ተከብሮ ሠራተኛው መላ ጉልበቱን ችሎታውን በሥራ ላይ አውሎ ምርት የሚያግድበትና የሚሻሻልበትን ሁኔታዎች አስመልክቶ ድርጅቱ የሚወሰደውን እርምጃ ተግባራዊ እንዲደረግ ጥረት ማድረግ፡፡ 
  3. የሠራተኛ ማኅበሩን አባላት ወይም የፋብሪካውን ሥራ ሚመለከቱ በሠራተኛ ማኅበሩ በኩል የሚለጠፉ ወይም የፋብሪካውን ሥራ የሚመለከቱ ማስታወቂያዎች ከመውጣቱ በፊት ከፋብሪካው አስተደዳደር ጋር ተነጋግሮ መለጠፍ ይችላል፡፡ 
  4. በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ የፋብሪካውን አስተዳደር ሕጋዊ መብትና ክብሩን የሚነካ ወይም የሚቀንስ ተግባር አለመፈፀም፡፡ 
  5. በሠራተኛና በድርጅቱ መካከል ግጭትና /አለመግባባትን/ የሚፈጥር ወይም የሚያባብሱ ድርጊቶችን ከመፈፀም መቆጠብና ቅሬታዎች ሲነሱ በቅድሚያ በውይይትና በሥምምነት ለመፍታት መሞከር፡፡

አንቀጽ 11

የሠራተኛው መብቶች

  1. አንድ ሠራተኛ በሕክምና ላይ እነንዲቆይ ከተደረገ ይህንኑ ለሚመለከተው ክፍል በ2/ሁለት/ ቀን ውስጥ እንዲያውቀው ያደርጋል፡፡ ተገቢውን የሕክምና ማስረጃ ሲያቀርብ በአዋጁና በደንቡ መሠረት ደመወዝ ይከፈለዋል፡፡
  2. በመሣሪያው ብልሽት ሠራተኛው የሚሠራው ሥራ ቢበላሽ ሠራተኛው ጥፋተኛ እስካልሆነ ድረስ ለብልሽቱ ኃላፊ አይሆንም፡፡ 
  3. ሴት ሠራተኞች ወደ ሥራ ሲገቡና ሲወጡ በሴት ፈታሾች ብቻ ይፈተሻሉ፡፡ 
  4. ከሥራ በተገናኘ ሁኔታ ጤንነቱና ደህንነቱ ተጠብቀውለት ስራውን ለማከናወን፡፡ 
  5. ሥልጠናና ትምህርትን በሚመለከት በአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ አዋጅ 377/1996 እና በፋብሪካው ባለው ደንብ መሠረት ይፈፀማል፡፡ 
  6. በሠራተኛው ጥፋት ወይንም በቸልተኝነት ሳይሆን በመሣሪያ ብልሽት ወይም በጥሬ ዕቃ ዕጥረት ሠራተኛ ሣይሠራ ቢውል ሠራተኛ መደበኛ ደመወዙን ይገኛል፡፡ 
  7. በሕግ፣ በሕብረት ሥምምነት ወይንም በሥራ ደንብ በተወሰነ ወይም በፍርድ ቤት ትዕዛዝ ካልሆነ ወይም ሠራተኛው በፅሁፍ ካልተስማማ በስተቀር አሠሪው ከሠራተኛው ደመወዝ ሊቀንስ ወይም በዕዳ ሊይዝ ወይም ሊያቻችል አይችልም፡፡
  8. ከመንግስት ሕጎችና መመሪያዎች በሠራተኛና አሠሪ ጉዳይ አዋጅ በሠራተኛ ማኅበራት በዚህ ሕብረት ሥምምነት ውስጥ በዝርዝር የተጠቀሱትን መብቶችና የሥራ ሁኔታዎች ለፋብሪካው ሠራተኞች ሁሉ የተጠበቀ ይሆናል፡፡ 
  9. የሚገባውን ደመወዝና ሌላም ሕጋዊ ክፍያ በየጊዜው በወቅቱ የማግኘት፡፡ 
  10. ማንኛውም የፋብሪካ ሠራተኛ በማህበሩ አማካኝነት ወይም በግሉ ቅሬታን ወይም ክርክሩን በአዋጅ 377/1996 መሠረት ሕጋዊ መብቱን ሊያስከብር ይችላል፡፡ 
  11. ተመሣሣይ ሥራ የሚሠሩ ሠራተኞች ችግር የሚገጥማቸው ጊዜ የክፍል ኃላፊው አምኖበት ሲፈቅድ ብቻ ሽፍታቸውን ተቀያይረው መሥራት ይችላሉ፡፡  
  12. ማናቸውም ቋሚ ሠራተኛ እራሳቸውን ለማሻሻልና ለመምራት ይችሉ ዘንድ በሚፈጠረው ክፍት የሥራ ቦታ መመዘኛውን ካሟሉ መወዳደር መብት አላቸው፡፡ 
  13. የአዲስ ተቆጣሪ ሠራተኛ መነሻ ደመወዝና ጥቅም በሠራተኛውን በአሠሪው መካከል በሚፈለገው የሥራ ውል መሠረት ይሆናል፡፡ 
  14. የመሥሪያ መሣሪያዎችና ጥሬ ዕቃዎች በወቅቱ ቀርበውለት ስራውን ለማከናወን 
  15. የአደጋ መከላከያና የሥራ ልብሶችን በዚህ ሕብረት ሥምምነት መሠረት በተወሰነ ጊዜ ማግኘት 
  16. የተቀጠረበት ቀን፣ የወር ደመወዝ ልክ፣ የት/ት ማስረጃ፣ የተከታተላቸው ሙያ አይነቶችና የሥራ ልምድ እንዲሁም አስፈላጊ የሆኑ የሕይወት ታሪክ ማስረጃዎች በጥንቃቄ በግል ማኅደር ውስጥ እንዲጠበቁለት፣ 
  17. ከሥራ ሲሠናበት ሕጋዊ የሆነ ምሥክር ወረቀት ለማግኘጥ፡፡ 
  18. የሕብረት ሥምምነቱና አዳዲስ መመሪያዎችና ደንቦች ሲወጡ በትክክል ተገንዝቦ ለመጠቀም 
  19. በሥራ የደከመን አእምሮ አዝናንቶ ወደ ሥራው ሚመለስበትን ዓመት ዕረፍት ፈቃድ ፕሮግራም ለማግኘት 
  20. የግልና የሥራ ልብሱን የሚያስቀምጥበትን ቦታ የማግኘት 
  21. በመመገቢያና በሥራ ሠዓት መካከል ትርፍ ጊዜው የመዝናኛ ቦታ ከድርጅቱ ጋር በመመካከር የማግኘት መብት፡፡ 
  22. አንድ ሠራተኛ የቤተሰብ ውስጥ/ሕጋዊ ሚስት ወይም ባል እነንዲሁም አዲስ የሚወለዱ ልጆች በሚያደርግበት ጊዜ በወቅቱ በሕይወት ያሉትን ማስመዝገብ ይችላል፡፡ 

አንቀጽ 12

የሠራተኛው ግዴታዎች

  1. በቅልጥፍናና በተሟላ ትጋት ሥራውን ማከናወን፣ 
  2. የሕብረት ሥምምነቱንና የፋብሪካውን የሥራ ማሻሻያ መተዳደሪያ በሚገባ ማክበርና በትክክል መፈፀም፡፡ 
  3. ለፋብሪካው ጥቅም ሲባል ወይም ሠራተኛ በሚሠራበት ቦታ ያለው ስራ ቢያንስ ወይም ቢቀንስ ፋብሪካው የሠራተኛውን ብቁነት በማገናዘብ በተመሣሣይ ስራ መደብ ሊያሰራ ይችላል፡፡ ሆኖም በምደባው ምክንያት የሠራተኛው ደመወዝ ወይም ደረጃ ሊቀንስበት አይችልም፡፡ 
  4. ሊታለፍ የማይችል አስገዳጅ ግዴታ ካልደረሰበት በስተቀር አስቀድሞ ሳይጠይቅ ከሥራ አለመቅረት፡፡ ለዚሁም ማስረጃ ማቅረብ አለበት፡፡ 
  5. ለራሱና ለፋብሪካው ጥሩ ሥም በሚያስገኝ መንገድ ሁልጊዜ ራሱን መምራት 
  6. ሠራተኛው ለራሱ አገልግሎት እንዲጠቀምባቸው የተሠጡትን ዕቃዎች፣ መሣሪያዎች፣ መኪናዎችና ሌሎች ንብረቶችን በሚገባ መያዝና መንከባከብ አለበት፡፡ 
  7. በራሱና በሥራ ባልደረቦቹ ወይም በሌሎች ሠዎች እንዲሁም በፋብሪካውና በመሣሪያ ዕቃዎች ላይ አደጋ ከሚያመጡ ነገሮች መጠበቅና መጠንቀቅ ጉዳት ወይንም አደጋ በፋብሪካው ወይም በሥራ ባልደረቦቹ ላይ በሚያጋጥም ጊዜ ዕርዳታ በተፈለገበት ቦታ ሁሉ መሥጠት፡፡ 
  8. ሠራተኞች በራሳቸው ፈቃድ ተነሳስተው የሥራ ለውጥ አያደርጉም፡፡  
  9. ለሥራ የመተባበር አንድነትን ማሣየት፣ 
  10. ማንኛውም ሠራተኛ ከሚመለከተው ኃላፊ የፅሁፍ ፈቃድ አስቀድሞ ሳይቀበል የፋብሪካው ንብረት የሆነውን ማንኛውንም ዓይነት ዕቃ እንዲሁም የተሠራ ወይንም ያልተሠራ ጨርቅ ከፋብሪካው ቅጥር ጊቢ ማውጣት ወይም በማናቸውም ምክንያት ለራሱ አገልግሎት ማዋል አይችልም፡፡ 
  11. ሰራተኛው ቤተሰብ ነው በማለት ቤተሰቡ ያልሆነ ሌላ ሰው አስመዝግቦ ከተገኘ ማግኘት የሚገባውን አገልግሎት አያገኝም፡፡ 
  12. በፋብሪካውና በሠራተኛ ማኅበሩ ወይም በፋብሪካውና በሠራተኛው መካከል አለመግባባት የሚፈጥር ሀሰተኛ ወሬና ጠብ በማንሣት ወይንም ጠብ እንዲነሣ ከመገፋፋት በብርቱ መጠንቀቅ አለበት፡፡ 
  13. ያለበቂ ምክንያትና ያለፈቃድ በሥራ ሠዓት ከሥራ ገበታቸው ተለይተው ከቦታ ቦታ በመዘዋወር እራሳቸውም ሥራ ፈትተው ሌላውን ሥራ ማስፈታት እንዲሁም ያለ ፈረቃቸው ወደ ፋብሪካው ቅጥር ጊቤ በመግባትና መዘዋወር የለባቸውም፡፡ 
  14. ማንኛውም የፋብሪካው ሠራተኛ በምድብ ሥራው ላይ ሆኖ መተኛት የለበትም፡፡ 
  15. ማንኛውም ሠራተኛ የሥራ ሠዓቱን በመጠበቅና በማክበር አስቀድሞ መውጣት ወይም አርፍዶ መግባት የለበትም፡፡ 
  16. የጥበቃ ሠራተኞች ቀንም ሆነ ሌሊት በተመደቡበት ቦታና ሰዓት በንቃትና በተጠንቀቅ መገኘት አለባቸው፡፡ 
  17. ማንኛውም ሠራተኛ በአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ አዋጅ እና በሌሎች የመንግስት ሕጎች፣ ደንቦችና መመሪያዎች እንደዚሁም በዚህ ህብረት ሥምምነት የሥራ ውሉ የተመለከተውና በተጨማሪም በፋብሪካ የሚሠጠውን የተቀጠረበትን የሥራ መደብ ወይም (Job Discription) በሙሉ አክብሮ መቀበል አለበት፡፡ 
  18. የፋብሪካው የሥራ ውጤት እንዲዳብር ሥራውን በጥንቃቄ ማከናወንና ስለ ጤናው አጠባበቅ ስለ አደጋ መከላከያ ዘዴዎች የሚሠጡትን መመሪያዎች በጥንቃቄ ጠብቆ መሥራት አለበት፡፡      
  19. ማንኛውም ሠራተኛ በማንኛውም ዓይነት ፈቃድ ወይም በሕመም ወይም በማናቸውም ሕጋዊ ምክንያቶች አስቀድሞ በመጠየቅ ተፈቅዶለት ከመደበኛ ሥራ ላይ የቀረ ከሆነ ለሥራው የሚያገለግለውን በዕጁ የሚገኝ ዕቃ እንዲሁም በጅምር ላይ ያለን ሥራ ሁሉ ለቅርብ ኃላፊው ማስረከብ አለበት፡፡ 
  20. ደረጃውና ጥቅሙ ተጠብቆ ነገር ግን ለፋብሪካው ጥቅምና ዕድገት ሲባል የሚሠራበት ቦታ ወይም ፈረቃ እንዲዛወር ሲጠየቅ በፈቃደኝነት መፈፀም፣ ሥነ-ሥርዓት ማክበር፣ ትዕዛዝን በተገቢው መንገድ መፈፀም፣ ቅሬታ ሲኖር በሥነ-ሥርዓት መጠየቅ፡፡ 
  21. ማንኛውም ሠራተኛ ወደ ፋብሪካው ጊቢ ሲገባና ሲወጣ እርሱ ወይም የያዘው ተሸከርካሪ መፈተሽ አለበት፡፡ 
  22. በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የፋብሪካውን አስተዳደር ሕጋዊነት የሚቀንስ ወይንም የሚወስን ወይም ክብርን የሚነካ ሕገ-ተግባር አለመፈፀም፡፡ 
  23. ማንኛውም ሠራተኛ ታሞ ወደ ክሊኒክ ሔዶ የሕመም ፈቃድ ሲሠጠው የፈቃዱን ወረቀት ለቅርብ አለቃና ለሰዓት ቁጥጥር ማቅረብ አለበት፡፡ 
  24. በዚህ የሕብረት ሥምምነቶች በተጠቀሱት ሐኪም ቤቶች ተመርምሮና ታክሞ ሲመለስ የተሠጠውን የሐኪም ማስረጃ ማቅረብ ይኖርበታል፡፡ 
  25. ማንኛውም ሠራተኛ የተሠጠውን የሥራ ልብስ እና የአደጋ መከላከያ የልብስና የምግብ ማስቀመጫ ሣጥን በጥንቃቄ መያዝ አለበት፡፡ 

ክፍል 3

አንቀጽ 13

የአዲስ ሠራተኛ አቆጣጠር ሥነ-ሥርዓት

  1. አዲስ ሰራተኛ ሲቀጠር የሚችለው ከዚህ በታች በተመለከተው ምክንያቶች ነው፡፡ 
  1. ለፋብሪካው መስፋፋት ወይም ለምርት ዕድገት የተለያየ ሙያ የሚጠይቅ ተጨማሪ የሰው ኃይል አስፈላጊ መሆኑን ፋብሪካው ሲወሰን፣ 
  2. ተይዞ የነበረው ሥራ ተለቆ ከፋብሪካው ሠራተኞች ውስጥ ለሥራው አስፈላጊ ችሎታ ያለው ሰራተኛ ሲታጣ፣ 
  3. አዲስ ሥራ ቦታ ተከፍቶ ቦታውን የሚሸፍን ዕውቀትና ሙያ ያለው ሠራተኛ ከፋብሪካው ሠራተኞች ውስጥ ሲታጣ፣ 
  4. ለተወሰነ ስራ (ጊዜ) ሠራተኛ ሚቀጠርበት ሁኔታ ሲያጋጥም፣ 
  5. በሕጉ መሠረት የውጪ ሀገር ዜጋ መቅጠር ሲያፈልግ፣ 
  6. ከዚህ ውጪ የሆነ አቀጣጠር ሲያጋጥም በአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ አዋጅ 377/1996 እና በመንግስት መመሪያዎች መሠረት ተፈፃሚ ይሆናል፡፡ 

አንቀጽ 14

ከፋብሪካው የተሠናበተ ሠራተኛን መልሶ ስለመቅጠር

  1. አስቀድሞ በፋብሪካው ሥራ ላይ የነበረው ሠራተኛ የተሰናበተ ሠራተኛ መልሶ ለመቅጠር የሚቻለው በአሠሪና ሠራተኛ አዋጅ ቁጥር 377/1996 መሠረት ይሆናል፡፡ 
  1. ነባር የፋብሪካው ሠራተኛ መሆኑና የወጣበት ምክንያት ሳይሰውር በግልፅ ሲያቀርብ፣ 
  2. ፋብሪካው የሚያወጣውን መመዘኛ መሠረት ለፋብሪካው ሥራ ብቁና የተሟላ ችሎታ ያለው መሆኑ ፋብሪካው ሲያረጋግጥ፣ 
  1. አስቀድሞ በፋብሪካው ሥራ ላይ በነበረበት ጊዜ ከፋብሪካው የተሰናበተ ሠራተኛ የአገልግሎት ዘመን መቆጠር የሚጀምረው ተመልሶ በአዲስ መልክ ከተቀጠረበት ዕለት አንስቶ ነው፡፡ 

አንቀጽ 15

የሥራ ውል አመሠራረት

  1. አንድ ሠራተኛ ለፋብሪካው ሥራ ሲቀጠር ወይም ሲመደብ ከነበረበተት ሌላ ድርጅት ተዛውሮ ሲመጣ፣ 
  1. የሠራተኛ የሥራ መደብ ከሥራ ዝርዝር ጋር 
  2. የሥራ ቦታው 
  3. የሥራ ደረጃ 
  4. የሥራ ክፍል 
  5. የሥራ ውሉ የሚፀናበት ጊዜ 
  6. የሚከፈለው ደመወዝ 
  7. አበል ወይም ካሣ 
  8. የሙከራ ጊዜ 
  9. መብትን፣ ግዴታን እና ጥቅምን በሚመለከት ይህንኑ የሚገልፅ ደብዳቤ ይሰጠዋል፡፡ 
  1. በአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ አዋጅ 377/1996 እና ይህ የሕብረት ሥምምነቱ በተጨማሪም የመንግሥት በየጊዜው የሚያወጣቸውና ወደ ፊትም የሚያወጣቸው መመሪያዎች ከሥራ ውሉ እንደ አንዱ ክፍል የሚቆጠሩ ይሆናሉ፡፡ 
  2. ለሠራተኛው በሚሠጠው የቅጥር ደብዳቤ ላይ የሚገለፀው ከአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ ከአዋጅ እና ከሕብረት ሥምምነት ውጪ ለሠራተኛው ከተሠጠው መብትና ጥቅም ወይም ግዴታ የሚቀንስ ከሆነ ተቀባይነት አይኖረውም፡፡ 
  3. በአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ አዋጅ 377/1996 መሠረት ፋብሪካው ሠልጣኝ ሠራተኛ ሲቀጥር ከሠልጣኙ ጋር በፋብሪካው የሥልጠና ውል መሠረት የሚፈፀም ይሆናል፡፡    

አንቀጽ 16

የሥራ መልቀቂያና የምሥክር ወረቀት

  1. አንድ ሠራተኛ በዚህ ሕብረት ሥምምነት መሠረት ውል ሲፈፅም ወይም ሲቋረጥ የምሥክር ወረቀት ይሠጠዋል፡፡ 
  2. የምሥክር ወረቀት የሠራተኛ ፎቶ ግራፍ ያለበት ሆኖ ሠራተኛው የሚሠራውን ሥራ ሙያውን፣ የሠራበትን ዘመን፣ የሚያገኘውን ደመወዝና ከሥራ የለቀቀበትን ምክንያት የሚገልፅ መሆን ይኖርበታል፡፡ 
  3. የመንግስት ልዩ ታክሶችን የከፈለ መሆኑን የሚገልፅ፣ 
  4. የጡረታ መለያ ቁጥሩንና ልዩ ክፍዎችን የሚገልፅ ሆኖ የመሥሪያ ቤቱ ማኅተም ያረፈበትና የፋብሪካው የበላይ ኃላፊ የፈረመበት ይሆናል፡፡ 
  5. ይህም የምሥክር ወረቀት ለሠራተኛ የሚሠጠው በዕጁ የነበረውን ንብረት ወይም ገንዘብ ወይም ማንኛውንም ፋብሪካው የሚፈልግበትን ሁሉ ባስረከበ በ5 ቀን ውስጥ ይሆናል፡፡ 

አንቀጽ 17

የሙከራ ጊዜ 

  1. ማንኛውም አዲስ ተቀጣሪ ሠራተኛ የሙከራ ጊዜ ከ45 ተከታታይ ቀናት መብለጥ የለበትም፡፡ 
  2. በሙከራ ጊዜ ላይ ያለ ሠራተኛ ለስራው ብቁ ካልሆነ ፋብሪካው ያለምንም ማስጠንቀቂያና ካሣ ሊያሰናብተው ይችላል፡፡ 
  3. ለሙከራ የተቀጠረ ሠራተኛ የሙከራ ጊዜውን ጨርሶ ቋሚ ከሆነ የአገልግት ዘመኑ ለሙከራ ከተቀጠረ ጊዜ ጀምሮ ይሆናል፡፡ 
  4. ሠራተኛው የሙከራ ጊዜውን ካለቀ በኋላ ስራውን ከቀጠለ ሙከራውን አልፎ በውሉ መሠረት እንደተቀጠረ ይቆጠራል፡፡  
  5. በሙከራ ላይ ያለ ሠራተኛ ያለማስጠንቀቂያ ሥራውን ሊለቅ ይችላል፡፡ 

አንቀጽ 16

የሥራ ሠዓት

  1. በዚህ የሕብረት ሥምምነት ከተጠቀሰው መደበኛ የሥራ ሰዓት በላይ የሚሠራ ሁሉ የትርፍ ሰዓት ሥራ ይሆናል፡፡ 
  2. የትረርፍ ሰዓት ሥራ የሚሠራው አሠሪው በሚሠጠው ግልፅ ትዕዛዝ ብቻ ነው፡፡ 
  3. ማንኛውም ሠራተኛ በትርፍ ሰዓት ሥራ እንዲሠራ አይገደድም፡፡ ሆኖም አሠሪው ሌላ አማራጭ መንገድ ሊኖረው አይችል ተብሎ ሲገመትና፣ 

ሀ/ አደጋ ሲደርስ ወይንም አደጋ የሚደርስ መሆኑ ሲያሰጋ 

ለ/ ከአቅም በላይ የሆነ ሁኔታ ሲያጋጥም 

ሐ/ በአስቸኳይ የሚሠራ ሥራ ሲያጋጥም 

መ/ በሚያቋርጥና ከተከታታይ ሥራ ላይ ከሥራ የቀሩ ሠራተኞችን ለመተካት አሠሪው የትር ሰዓት ሥራ ለማሠራት ይችላል፡፡ 

  1. በአስቸኳይ የሚሰራ የትርፍ ሰዓት ስራ በቀን ከሁለት ሰዓት በወር ከ20 እና በዓመት ከ100 ሰዓት መብለጥ የለበትም፡፡ 
  1. የትርፍ ሠዓት አከፋፈል፡፡ 
  1. ከንጋቱ 12፡00 ሠዓት እስከ ምሽቱ 4፡00 ሠዓት የትርፍ ሠዓት ሥራ ለመደበኛ ሥራ በሠዓት ሚከፈለው ደመወዝ 1¼ ተባዝቶ፣ 
  2. ከምሽቱ 4፡00 ሠዓት እስከ ንጋቱ 12፡00ሠዓት ለሚሠራ ትርፍ ሠዓት ሥራ ለመደበኛ የሥራ ሠዓት የሚከፈለው ደመወዝ 1½ ተባዝቶ፣ 
  3. በሣምንት የዕረፍት ቀን ለሚሠራ የትርፍ ሠዓት ሥራ መደበኛ የሥራ ሠዓት በሠዓት የሚከፈለው ደመወዝ በ2 ተባዝቶ፣ 
  4. በሕዝብ በዓላት ለሚሠራው የትርፍ ሠዓት ለመደበኛ ሥራ በሠዓት የሚከፈለው ደመወዝ በ2 ½ ተባዝቶ፣ 
  5. ትርፍ ሠዓት ክፍያ የሚከፈለው ለደመወዝ መክፈያ በተወሰነ ቀን ነው፡፡ 

አንቀጽ 20

የሣምንት ዕረፍት ጊዜ 

      1. ማንኛውም ሠራተኛ በሰባት ቀናት ጊዜ ውስጥ ያልተቆራረጠ ከሃያ አራት ሰዓት የማያንስ ዕረፍት ያገኛል፡፡ 
      2. የሣምንት የዕረፍት ጊዜ በተቻለ መጠን 

      ሀ/ ዕሁድ ቀን ይውላል፡፡ 

      ለ/ ለድርጅቱ ሠራተኞች እንደየሥራ ባሕሪያቸው የዕረፍት ጊዜ ይሠጣል፡፡ 

      1. የሣምንት የዕረፍት ቀን ዕሁድ ቀን እንዲውል ለማድረግ ካልተቻለ በምትኩ ሌላ ቀን የሣምንት የዕረፍት ቀን ሊሆን ይችላል፡፡ ይህም የሚሆነው ከሥራው ባሕሪ ወይም በቴክኒክ ምክንያት ሊቋረጥ ወይም ለሌላ ጊዜ ቢተላለፍ ችግር ወይም ጉዳት የሚያስከትል ሥራ ሆኖ ሲገኝ ነው፡፡ 
      2. ከዚህ በታች በተመለከቱት ምክንያቶች የፋብሪካው መደበኛ ተግባር የሚያደናቅፍ ሁኔታዎች ለማስወገድ አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ ብቻ ሠራተኛውን በማንኛውም የዕረፍት ጊዜው እንዲሠራ ማድረግ ይቻላል፡፡ 

      ሀ/ ከአቅም በላይ የሆነ ሁኔታ ሲያጋጥም 

      ለ/ በአስቸኳይ የሚሠራ ሥራ ሲያጋጥም 

      1. ሠራተኛ የተጠቀሰው በምትክ የሚሠጥ የዕረፍት ጊዜ ሳይወስድ የሥራ ውሉ ቢቋረጥ በሠራው መጠን የማካካሻ ይሠጠዋል፡፡ 

      አንቀጽ 21

      የሠራተኛው የሥራ አፈፃፀም ምዘና

      1. የሥራ አፈፃፀም ምዘና በዓመት ሁለት ጊዜ ይሞላል፡፡ 
      2. የሥራ አፈፃፀም ምዘና ሪፖርት በሠራተኛው የቅርብ ሥራ ኃላፊ ተሞልቶ በቅርብ የበላይ ኃላፊ ተመርምሮ ለአስተዳደሩ ይላካል፡፡ 
      3. የሥራ አፈፃፀም ሪፖርት በሁለት ኮፒ ተሞልቶ አንደኛው ኮፒ በሠራተኛው የግል ማህደር ይቀመጣል፡፡ 2ተኛው ኮፒ ለዕድገት ሥልጠናና ሌሎች አስተዳደራዊ ክፍል ይቀመጣል፡፡ 
      4. በሥራ አፈፃፀም ምዘናው 3.5 እና ከዚያ በላይ ውጤት የሌለው ሠራተኛ ለዕድገት ውድድር ሊቀርብ አይችልም፡፡ 
      5. ኃላፊነት፡- 
      1. የሥራ አፈፃፀም ምዘና ሪፖርት በጥንቃቄና በትክክል የመሙላት፣ 
      2. ማንኛውም ሠራተኛ የሥራ አፈፃፀም ሪፖርቱን ተመልክቶና አስተያየት ሠጥቶበት እንዲፈርም የማድረግ፣ 
      3. በሥራ አፈፃፀም ምዘና ሪፖርት አማካይ ከአራት ነጥብ አምስት/4.5/ በላይ እና ከሁለት ነጥብ አምስት /2.5/ በታች ላገኘ ሠራተኛ ይኸው ነጥብ ሊሠጠው የቻለበትን ምክንያት በዝርዝር የመግለፅ የሥራ አፈፃፀም ምዘና ሪፖርት የሚሞላው ኃላፊ ሃላፊነት ነው፡፡ 
      4. የድርጅቱ ሠራተኞች በሙሉ ደረጃ እንዲሠጣቸው ወይም በድርጅቱ ውስጥ የሥራ ደረጃ መኖር አለበት፡፡ 

      አንቀጽ 22

      ደመወዝና ልዩ ልዩ ክፍያዎች

      1. የደመወዝ አከፋፈል 
      1. የጠቅላላ ሠራተኛ ደመወዝ በወሩ እ.ኤ.አ በ28ኛው ቀን ይከፈላል፡፡ ሆኖም ይህን በሣምንት የዕረፍት ቀን ወይም በዓል ላይ የሚውል ከሆነ አስቀድሞ ባለው የሥራ ቀን እንዲከፈል ይደረጋል፡፡ 
      2. ደመወዝ የሚከፈለው በቀጥታ ለሠራተኛ ሲሆን በልዩ ልዩ ምክንያቶች ቀርቦ መቀበል ካልቻለ ግን በፅሁፍ ቤተሰቡን ወይም በፋብሪካው ውስጥ ሠራተኛ የሆነ ጓደኛውን ወክሎ ማኅበሩ አረጋግጦ ለአስተዳደር ሊያስተላልፍና ለወኪሉ ሊከፈለው ይችላል፡፡ 
      3. አንድ ሠራተኛ በወር ውስጥ ተመላሽ የሚሆን ደመወዝ አንድ ሦስተኛ 1/3 ቅድሚያ ደመወዙን ወይም ሳለሪ አድቫንስ ማግኘት ይችላል፡፡ አከፋፈሉም ተፈፃሚ የሚሆነው ወር በገባ በስምንተኛው ቀን ይሆናል፡፡ በተጠቀሰው ጊዜ አድቫንስ ያልወሰደና ድንገተኛ ችግር ላጋጠማቸው ሠራተኞች ሁኔታው እየታየ እስከ 15ተኛው ቀን ሊከፈላቸው ይችላል፡፡ 
      4. ለገንዘብ ከፋይ የሚሠጥ የማካካሻ አበል በተመለከተ በሚመለከተው የገንዘብ መጠን ላይ የተመሠረተ ይሆናል፡፡ 
      1. የማበረታቻ ክፍያ (ኢንሴንቲቭ)
      1. ፋብሪካው ለምርት ዕድገት አስፈላጊ ሆኖ ሲያገኘው እንደ አስፈላጊነቱ በቡድንም ሆነ በተናጠል የማበረታቻ ክፍያ ሥርዓት በማጥናት ወይንም በማስጠናት ክፍያ ሊፈፅም ይችላል፡፡ 
      2. ፋብሪካው በተራ ቁጥር 2.1 የተጠቀሰውን ለማኅበሩ ቅድሚያ እንዲያውቀው ያደርጋል፡፡ 

      አንቀጽ 23

      የውሉ አበል አከፋፈል

      1. ማንኛውም የፋብሪካው ሠራተኛ በሥራ ጉዳይ ፋብሪካው ካለበት ወይም ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ካለበት ከተማ ከ30ኪ.ሜ ውጪ በሚሄድበት ጊዜ የውሉ አበል ይከፈለዋል፡፡ ፋብሪካው ለዚሁ ተግባር የትራንስፖርት አገልግሎት ማቅረብ ካልቻለ ሠራተኛ በመንገድና ትራንሰፖርት ደረሠኝ መሠረት ይከፈለዋል፡፡ የ30ኪ.ሜ ገደብ ግን በትራንሰፖርት ክፍያ ላይ ተፈፃሚ አይሆንም፡፡ 
      2. ዕለታዊ የአበል አከፋፈል በመቶኛ እንደሚከተለው ይሆናል፡፡ ይኸውም ለቁርስ 10 በመቶ (10)፣ ለምሣ ሃያ አምስት በመቶ (25)፣ ለዕራት ሃያ አምስት ከመቶ (25) ሆኖ ዕለታዊ የአበል ክፍያ ከዚህ በታች እንደሚከተለው ይሆናል፡፡ ደመወዛቸው፡- 
      • 600 እስከ 800 ለሆኑ በቀን ብር 150.00 /አንድ መቶ ሃምሳ ብር/
      • 901 እስከ 1200 ለሆኑ በቀን ብር 160.00 /አንድ መቶ ስልሣ ብር/     
      • 1201 እስከ 1400 ለሆኑ በቀን ብር 170.00 /አንድ መቶ ሰባ ብር/
      • 1401 እስከ 1600 ለሆኑ በቀን ብር 180.00 /አንድ መቶ ሰማኒያ ብር/  
      • በ1601 በላይ ለሆኑ በቀን ብር 200.00 /ሁለት መቶ ብር/

        አንቀጽ 24

        የደረጃና የደመወዝ ዕድገት አሠጣጥ

        1. የደረጃ ዕድገት ማለት በሕብረት ሥምምነት መሠረት ከዝቅተኛ የሥራ መደብ ወደ ከፍተኛ የሥራ መደብ የሚደረግ ምደባ ነው፡፡ 
        2. የደረጃ ዕድገት የሚሠጠው ነባር ሠራተኛ ከሥራ መደቡ በዕድገት፣ በዝውውር ወይም በሌላ ምክንያት ሲለይ የሚፈጠሩትን ክፍት የሥራ ቦታዎች ለመሙላትና የፋብሪካው ስራ በመሥፋቱ ምክንያት የሚፈጠሩትን ክፍት የሥራ መደቦች ከፋብሪካው ውስጥ ካሉት ቋሚ ሠራተኞች አወዳድሮ ለመሙላት ነው፡፡ 
        3. ክፍት የሥራ መደቡ ዕድገት እንዲሞላ ሲፈቀድ ለተጠቀሰው የሥራ መደብ የሚያስፈልገውን የትምህርት ደረጃ፣ የሥራ ልምድና ሌሎችም አስፈላጊ መረጃዎች ይወጣል፡፡ 
        4. በተራ ቁጥር 3 ላይ እንደተመለከተው ማስታወቂያ ለወጣበት ክፍት የስራ ቦታ አስፈላጊው አሟልተው ለተገኙ ሠራተኞች እንደአስፈላጊነቱ የጽሁፍ፣ የተግባር ፈተና ወይም የቃለ መጠይቅ ወይም ሦስቱም ተሠጥቶ ከዕጩዎቹ መካከል በአጠቃላይ ውጤት ለሥራው ይመጥናሉ ተብሎ የታመነበትን ሠራተኛ ዕድገቱን ሊያገኝ ይችላል፡፡ 
        5. የደረጃ ዕድገት ማጣራቱን ውድድር ተጠናቆ በፋብሪካው ዋና ሥራ አስኪያጅ ከፀደቀበት ቀን ጀምሮ እስከ አስራ አምስት ቀን ድረስ ለተወዳዳሪዎች በይፋ ይገለፃል፡፡ 
        6. አንድ ሠራተኛ በዕድገት የተመደበበትን የሥራ መደብ ላይ ቢያንስ ቢያንስ ለአስራ ሁለት ወራት ሳያገለግል በሌላ አዲስ የዕድገት ቦታ ለመወዳደር አይችልም፡፡ 
        7. የሠራተኛ ዕድገት ጉዳይ በሚታይበት ጊዜ ማሕበሩ በአባልነት ይገኛል፡፡ 

        አንቀፅ 25

        የጡረታ መብት አጠባበቅ

        1. ማንኛውም ሠራተኛ የጡረታ አዋጆች በሚፈቅዱበት መሠረት የጡረታ መብቱ ይጠበቅለታል፡፡  
        1. የፋብሪካው ሠራተኛ በጡረታ ለመገለል አንድ ዓመት ሲቀረው ፋብሪካው ለሠራተኛው ያሳውቃል ወይም ማስጠንቀቂያ ይሠጣል፡፡ 
        2. ሠራተኛው በጡረታ እንደሚገለል ማስጠንቀቂያ ሲደርሰው የማስጠንቀቂያው ኮፒ ለሠራተኛ ማኅበሩም እንዲደርሰው ይደረጋል፡፡ የጡረታ መቀበያ ደብተሩንም በወቅቱ እንዲያገኝ ፋብሪካውና የሠራተኛ ማህበሩ ጥረት ያደርጋሉ፡፡ 

        አንቀፅ 26 

        የሥራ ስንብት

        1. የሥራ ሥንብት ክፍያ የሚወሰደው በአሠሪና ሠራተኛ አዋጅ 377/1996 እና በዚህ ሕብረት ሥምምነት ብቻ ነው፡፡  
        2. የፋብሪካው ቋሚ ሠራተኛ ሊሠናበት የሚችለው፡፡ 
        1. የሥራ ስንበት ጥያቄ ከሠራተኛው ከቀረበና የሠራተኛው የሥራ ፀባይ ርክክብ የሚጠይቅ ከሆነ የማረካከቢያ ጊዜ ይሰጠዋል፡፡ በርክክብ ለቆየበት ጊዜ ደመወዝ ይከፈለዋል፡፡ 
        2. ሠራተኛው በራሱ ፈቃድ ስራውን ለመልቀቅ ጥያቄ አቅርቦ የመረካከቢያ ጊዜው መጠበቅ ካላስፈለገ እና በሠራተኛው ሥራ መልቀቅ የፋብሪካው ስራ የማይበደል መሆኑን ፋብሪካው ካመነበት በዕጁ የሚገኘውን ንብረት ተረክቦ ሠራተኛውን ወዲያውኑ ሊያሰናብተው ይችላል፡፡ የሚገባውን የአገልግሎት ካሣና ያልተጠቀመበት የዓመት ዕረፍት ፈቃድ ወደ ገንዘብ ተለውጦ ሠራተኛ ፋብሪካው ውስጥ በሠራባቸው ጊዜያት ለጎደላቸውና ላላወራረዳቸው ንብረቶች፣ አልፎም የተለያየ ብድሮችን ተቀንሶ በአምስት ቀናት ውስጥ ሊከፈለው ይገባል፡፡ 
        1. የሥራ ውል የሚቋረጥበት ሁኔታ  

        ማንኛውም የሥራ ውል በአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ አዋጅ 377/1996 እና በዚሁ የሕብረት ሥምምነት በተጠቀሱት ምክንያቶች የሚቋረጥ ሲሆን የሚከተሉትን ይጨምራል፡፡ 

        1. ሁለቱ ተዋዋይ ወገኖች ውሉን ለማቋረጥ ሲስማሙ፣ 
        2. ሠራተኛው ከሥራ ጋር ግንኙነት የሌለው ሕመም ምክንያት ስራውን ከ6 /ከስድስት/ ወር ለበለጠ ጊዜ ሲያቋርጥ፣ 
        3. ሠራተኛው ሲሞት፣ 
        4. ድርጅቱ በመክሰር ወይም በሌላ ምክንያት ስራው ለዘለቄታው ሲዘጋ፣ 
        5. የድርጅቱ ሥራ በመቀዝቀዙ ምክንያት ሠራተኛ ከድርጅቱ ማዛወር ሳይቻል ቀርቶ በቅነሣ ከሥራ እንዲወጣ ሲደረግ፡፡ 
        6. የሕብረት ሥምምነቱ መሠረተ ሠራተኛው ከሥራ የሚያስወጣ ጥፋት ሲፈፅም፣ 
        7. ሠራተኛው ስራ ለመልቀቀው ሲፈልግ፡፡ 
        8. ሠራተኛው በጡረታ ሲገለል
        9. ሠራተኛው የተመደበበትን ሥራ ለማከናወን ችሎታው ቀንሶ ሲገኝ ወይም የሥራ ችሎታውን ለማሻሻል አሠሪው ያዘጋጀለት ትምህርት እድል ባለመቀበሉ ምክንያት ሲሰራ የቆየውን ሥራ ለመቀበል የሥራ ችሎታ የሌለው ሆኖ ሲገኝ ወይም ትምህርት ከተሠጠው በኋላ አስፈላጊውን አዲስ የሥራ ችሎታ ለመልመድ የማይችል ሲሆን፣ 
        10. ሠራተኛው በጤንነቱ መታወክ ወይም በአካል ጉዳት ምክንያት በሥራ ውሉ የተጣለበትን ግዴታ ለመፈፀም ለዘለቄታው የማይችል ሆኖ ሲገኝ፣ 
        11. ሠራተኛው የያዘው የሥራ መደብ በበቂ ምክንያት ሲሰረዝና ሠራተኛው ወደ ሌላ ስራ መደብ ማዛወር የማይቻል ሲሆን፡፡ 
        1. የአገልግሎት ካሣ አከፋፈል፡፡ 
        1. አንድ ዓመት ያገለገል የአንድ ወር ደመወዝ ከአንድ ዓመት በታች ያገለገለ የሙከራ ጊዜውን የጨረሠ ሠራተኛ ግን እንደ አገልግሎቱ ጊዜ እየተተመነ ተመጣጣኝ ክፍያ ያገኛል፡፡     
        2. ከአንድ ዓመት በላይ ላገለገለ ለእያንዳንዱ ተጨማሪ ዓመት የደመወዙን አንድ ሦስተኛ 1/3 እየታከለ ይከፈለዋል፡፡ ሆኖም በማንኛውም ጊዜ የአገልግሎት ካሣ ክፍያ ከሠራተኛው የአንድ ዓመት ደመወዝ መብለጥ የለበትም፡፡ 

          አንቀጽ 27

          ማንኛውም ጥቅም የመጠየቂያ ጊዜ

          1. ደመወዝ ወይንም ማንኛውንም ክፍያ መጠየቅ ከሚገባው ጊዜ አንስቶ እስከ 6 /ስድስት/ ወር ድረስ ካልተጠየቀ በአሠሪና ሠራተኛ አዋጅ ቁጥር 377/1996 መሠረት በይርጋ ቀሪ ይሆናል፡፡ 

          አንቀጽ 28

          የትራንስፖርት አበል

          1. ድርጅቱ ለሠራተኞች የትራንስፖርት አበል ይከፍላል፡፡ አበሉ የእያንዳንዱ ሠራተኛ የወር ደመወዝ እየተሰራበት ባለው የደሞዝ ስኬል አከፋፈል ሆኖ ዝቅተኛው 200 መቶ ብር ከፍተኛው ደግሞ 950 ብር ይሆናል፡፡ 
          2. ማንኛውም የሙከራ ጊዜውን የጨረሰ ሠራተኛ የትራንስፖርት አበል ይከፈለዋል፡፡ 
          3. ሠራተኛው በሥራ ላይ ላልተገኘበት ጊዜ የትራንሰፖርት አበል አይከፈለውም፡፡ 

          አንቀጽ 29 

          ልዩ ልዩ ፈቃዶች 

          ክፍል 5 

          የዕረፍት ፈቃድ አሠጣጥ ሁኔታዎች   

          1. ዓመት ዕረፍት ፈቃድ 
          1. አንድ ሰራተኛ የዓመት ፈቃዱን በሚወስድበት ጊዜ የዕረፍት ጊዜ ጨምሮ ለሠራበት የሚገባውን ደመወዝ በቅድሚያ ማግኘት አለበት፡፡ 
          2. አንድ ዓመት ያገለገለ ሠራተኛ አሥራ አራት (14) የሥራ ቀን የዓመት ዕረፍት ፈቃድ ያገኛል፡፡ 
          3. ከአንድ ዓመት በላይ ያገለገለ ሠራተኛ በንዑስ ቁጥር 1.2 ከተመለከተው ቀን በላይ ላገለገለበት ለእያንዳንዱ ተጨማሪ ዓመት አንድ (1) የስራ ቀን ተጨማሪ እያታከለበት የዓመት ፈቃዱን ያገኛል፡፡ 
          4. አንድ ሠራተኛ ያገለገለበት ጊዜ ከአንድ ዓመት በታች ከሆነ የሙከራ ጊዜውን ከጨረሰ በአገልግሎት ዘመኑ ልክ ተመጣኝ የሆነ ዕረፍት በዚያው ባገለገለበት ዓመት ይሰጠዋል፡፡ 
          5. በዓመት ፈቃድ ላይ የሚገኝ ሠራተኛ የሚከፈለው ደመወዝ ሥራ ላይ ሆኖ ቢሆን ኖሮ ሊከፈለው ከሚገባው ጋር እኩል ይሆናል፡፡        
          6. ለዓመት ፈቃድ ብቁ የሚያደርገውን የአገልግሎት ጊዜ ለመወሰን ሲባል በድርጅቱ ለቀናት የሠራ ሠራተኛ ለአንድ ወር እንደሠራ ይቆጠራል፡፡ 
          7. በዚህ አዋጅ መሠረት የስራ ውሉ የተቋረጠ ሠራተኛ ያልወሰደው የዓመት ፈቃድ ታስቦ በገንዘብ ይሰጠዋል፡፡ 
          8. የዓመት ፈቃድ ስለመከፋፈልና ስለማስተላለፍ 
          1. ሠራተኛው የዓመት ዕረፍት ተከፋፍሎ እንዲሠጠው ሲጠይቅና አሠሪው ሲስማማ ለሁለት ተከፍሎ ሊሰጠው ይችላል፡፡ እንዲሁም ሠራተኛ ድንገተኛ ችግር ሲያጋጥመው ክፍሉ ሥራውን የማይበደል መሆኑን ካመነበት ከዓመት ፈቃድ የተቀነሰ ቀን ሊፈቀድለት ይችላል፡፡ 
          2. የዓመት ፈቃድ ሠራተኛው ሲጠይቅና አሠሪውም ሲስማማ ሊተላለፍ ይችላል፡፡ 
          3. አሠሪው የሥራ ሁኔታ ሲያስገድደው የሠራተኛውን የፈቃድ ጊዜ ሊያስተላልፍ ይችላል፡፡ 
          4. የተላለፈው የዓመት ፈቃድ ከሚቀጥለው ሁለት ዓመት በላይ ሊራዘም አይችልም፡፡
          1. ስለ ፈቃድ አሠጣጥ 
          1. አንድ ሠራተኛ ከአንድ ዓመት አገልግሎት ጊዜ በኋላ የመጀመሪያውን ዓመት ፈቃድ ከዚያም በኋላ በእያንዳንዱ ዓመት ተከታታዮች የዓመት ፈቃድ ያገኛል፡፡ 
          2. ፋብሪካው በሚያወጣው የዓመት ፈቃድ ምርጫ ፕሮግራም መሠረት በእያንዳንዱ ዓመት የሚያገኘው የዓመት ፈቃድ ለሠራተኛው ይሠጠዋል፡፡ 
          3. የሚወጣው ፕሮግራም 

          ሀ/ በእያንዳንዱ ሠራተኛ ፍላጎት 

          ለ/ ፋብሪካው ሥራውን ለተለመደ ሁኔታ እንዲሠራ ማድረግ አስፈላጊ መሆኑ በተቻለ መጠን በማገናዘብ ይሆናል፡፡ 

          ሐ/ አንድ ሠራተኛ ተገቢውን የዓመት ፈቃድ ወስዶ በዕረፍት ላይ እያለ ቢታመም ወይም ሴት ሠራተኛ በወሊድ ፈቃድ ሲሰጥ፣ የዓመት ዕረፍት ፈቃድ ወይንም የወሊድ ፈቃድ በዚያው መጠን ይራዘማል፡፡ 

          1. በፈቃድ ላይ ያለ ሠራተኛን ስለመጥራት፣ 
          1. በፈቃድ ላይ ያለን ሠራተኛ ለመጥራት የሚቻለው ቀደም ብሎ ሊታወቅ የማችል ምክንያት በሥራ ላይ መገኘት ያለበት ሲሆን ነው፡፡ 
          2. ሠራተኛ ከፈቃድ ሲጠራ በጉዞ ያጠፋው ጊዜ ሳይቆጠር የቀረውን የዓመት ፈቃድ በገንዘብ ተተምኖ ሊከፈለው ይችላል፡፡ 
          3. ሠራተኛው ፈቃዱን በመጠራቱ ምክንያት የደረሰበትን መጓጓዣና የውሎ አበል ወጪ ፋብሪካው ይችላል፡፡ 
          1. የወሊድ ፈቃድ 
          1. ማንኛውም ነፍሰጡር የሆነች ሴት ከእርግዝናዋ ጋር በተያዘ ምርመራ ለማድረግ ሐኪም በሚያዘው መሠረት ደመወዝ የሚከፈልበት ፈቃድ ይሰጣታል፡፡ ሆኖም የሕክምና ማስረጃውን ለአሠሪው ማቅረብ አለባት፡፡ 
          1. ነፍሰጡር የሆነች ሠራተኛ እወልዳለሁ ብላ ከገመተችበት ቀን በፊት መውለጃዋ ሲደርስ የ30 ቀን ተከታታይ ቀናት የወሊድ ፈቃድ እንዲሁም ስትወልድ ከወለደችበት ቀን ጀምሮ 60/ስልሣ/ ተከታታይ ቀናት የወሊድ ፈቃድ ከሙሉ ክፍያ ጋር ይሠጣታል፡፡ ነገር ግን ሠራተኛዋ ከመውለዷ በፊት የወለደችው የ30 ቀን ፈቃድ ቢያበቃና ካልወለደች እስከምትወልድበት ቀን ድረስ ሐኪም እንድታርፍ ካዘዘ ከክፍያ ጋር እረፍት ይሰጣታል፡፡  
          1. የወሊድ ፈቃድ ደመወዝ አከፋፈል፡፡ 

          ሀ/ ከመወውለጃዋ በፊት የሚሠጠው የ30 ቀን ፈቃድ ከደመወዝ ጋር ይሆናል፡፡ 

          ለ/ ከወለደች በኋላ የሚሠጣት የ60 ቀናት ፈቃድ ደመወዝ ፈቃድ በተጀመረበት ዕለት በወኪሏ አማካይነት ይሆናል፡፡   

          1. ነፍሰጡር የሆነች ሠራተኛ በዕርግዝናዋ ምክንያት ወይም ከወለደች በኋላ እስከ ስድስት ወር ድረስ የምትሠራው ሥራ ለጊዜው እንዲቀልላት ወይም እንዲለወጥ ሐኪም ሲያዝ ለጤንነቷ ተስማሚ የሆነ ሌላ ቀላል ሥራ ይሰጣታል፡፡ 
          2. በዚህ ሕብረት ሥምምነት የተመለከቱትን መብቶች ለማግኘት እንዲያስችል የፋብሪካው ሴት ሠራተኛ ወዲያውኑ ለፋብሪካው ክሊኒክ ማስመዝገብ አለባት፡፡ 
          3. ነፍሰጡር መሆኗን በሐኪም የተረጋገጠ ሠራተኛ ከምሽቱ 4/አራት/ሰዓት በኋላ እንድትሰራ አትችልም፡፡ በተጨማሪም የትርፍ ሰዓት ሥራ እንድትሠራ ግዴታ የለባትም፡፡ 
          4. መውለጃዋ የተቃረበ ሠራተኛ በሠዓት ላይ ሠራተኛ ከመውጣቱ በፊት 10 ደቂቃ ቀደም ብላ እንድትወጣ ይፈቀድላታል፡፡ 
          5. ሠራተኛዋ ያረገዘችው ፅንስ በራሷ ፍላጎት ሳይሆን በሌላ ምክንያት ቢያስወርዳት ከሒም በተሠጣት የፈቃድ ማስረጃ መሠረት ፈቃድ ከደመወዝ ጋር ይሠጣታል፡፡ 
          6. ነፍሰጡር የሆነች ሰራተኛ ወልዳ ልጇ ታሞ ሆስፒታል ከተኛና ሠራተኛዋ እንድታስታምም ሐኪም ሲፈቅድላት ደመወዝ የማይታሰብበት ፈቃድ ይሠጣታል፡፡ 
          7. ነፍሰጡር የሆነች ሠራተኛ በሥራ ላይ እያለች በደረሰ አደጋ ምክንያት ቢያስወርዳት ከሥራ ጋር በተያያዘ አደጋ ሀኪም በሚሠጠው ማስረጃ መሠረት ሙሉ ደመወዝ ከፈቃድ ጋር ይሰጣታል፡፡ 
          1. የጋብቻ ፈቃድ 
          1. ሙከራ ጊዜውን ያጠናቀቀና ሕጋዊ ጋብቻ ለሚፈፅም ለአንድ ጊዜ ብቻ ደመወዝ የሚከፈልበት ሶስት (3) የስራ ቀን ፈቃድ ይሰጠዋል፡፡ 
          2. የፋብሪካው ሠራተኛ ወንድም ሆነ ሴት ልጅ ሲድር እንዲሁም በራሱ ኃላፊነት የሚያሳድገው ጭምር ይኸውም አስቀድሞ ፋብሪካው በሚያዘጋጀው ፎርም አስመዝግቦ ሲገኝ ደመወዝ የሚከፈልበት (2) ሁለት ቀን ፈቃድ ይሰጠዋል፡፡ 
          3. ሚዜ ለሚሆን ሠራተኛ ደመወዝ የማይከፈልበት የ(3) ሦስት ቀን ነፃ ፈቃድ ይሠጠዋል፡፡ 
          4. በተራ ቁጥር 3.1 እስከ 3.3 ለተጠቀሰው ፈቃድ ሠራተኛው ቢያንስ ከ5 ቀናት በፊት ለክፍል ኃላፊው ማሳወቅ አለበት፡፡ 
          1. የሐዘን ፈቃድ 
          1. ሠራተኛው 

          ሀ/ የትዳር ጓደኛው፣ ወላጅ፣ ተወላጅ ወይም እስከ ሁለተኛ ደረጃ ድረስ የሚቆጠር የሥጋ ወይም የጋብቻ ዘመድ ሲሞትበት፣ ለሶስት የሥራ ቀናት ከክፍያ ጋር ፈቃድ ይሠጠዋል፡፡ 

          ለ/ እንዲሁም ከሠራተኛው መኖሪያ ቤት ውስጥ ሰው ሞቶ አስክሬን ከቤት ከወጣ ከክፍያ ጋር የአንድ ቀን ደመወዝ ይሰጠዋል፡፡      

          1. ሠራተኛው ልዩና አሳሳቢ ሁኔታ ሲያጋጥመው አስቀድሞ በፅሁፍ ሲጠይቅና ሲፈቀድለት እስከ አምስት ተከታታይ የሥራ ቀናት ፈቃድ የማግኘት መብት አለው፡፡ 
          2. ከላይ በተራ ቁጥር 1 የተመለከተው ሀዘን ሲደርስበት ሠራተኛው ለክፍል ኃላፊው እራሱ ወይም በመልዕክት በቅድሚያ አሳውቆ መሄድና ከሔደበት ቦታም በቂ ማስረጃ ማቅረብ አለበት፡፡ የማስረጃው ብቁነት የሚረጋገጠው በፋብሪካው አስተዳደር ነው፡፡ 
          3. ከላይ በተራ ቁጥር 1 ሀ የተሠጠው የፈቃድ የጊዜ መጠን እንዳለ ሆኖ ሠራተኛው ሄዶ የሚመለስበት የቦታ ርቀት ከ250 ከ/ሜትር ውጪ ከሆነ ከዓመት ዕረፍቱ የሚታሰብ የ5 ቀን የዓመት ዕረፍት ፈቃድ ይሠጠዋል፡፡ 
          1. የሕመም ፈቃድ 

          ለማንኛውም ሙከራ ጊዜውን የጨረሰ ሠራተኛ በሥራ ላይ ለሚደርስ ጉዳት ሳይሆን በሌላ ሕመም በዓመት የሚሠጠው የዓመት ፈቃድ እንደሚከተለው ይሆናል፡፡ 

          1. አንድ ወር ሙሉ ደመወዝ የሚከፈልበት፡፡ 
          2. ሁለት ወር ግማሽ ደወመዝ የሚከፈልበት፡፡ 
          3. ሶስት ወር ደመወዝ የማይከፈልበት ፈቃድ ይሠጣል፡፡ 
          4. ሠራተኛው በሕመም ምክንያት መሥራት አለመቻል በሐኪሞች ከተረጋገጠ ሠራተኛው ተገቢ መብቱ ተጠብቆለት ከሥራ ይሰናበታል፡፡  
          1. ይህ ሕመም ፈቃድ እንደ ሕጋዊ የዓመት ዕረፍት ፈቃድ ተቆጥሮ ለሌላው ዓመት አይተላለፍም፡፡ በገንዘብም አይለወጥም፡፡ 
          1. ለማኅበር ሥራ የሚሠጥ ፈቃድ 
          1. በጣም አስቸኳይ ካልሆነ በቀር ለማኅበሩ የሥራ አስኪያጅ ኮሚቴና አባሎች ማኅበሩ ከሃያ አራት (24) ሠዓት በፊት በፅሁፍ ሲጠይቅ ፋብሪካው እንደአስፈላጊነቱ ከደመወዝ ጋር ፈቃድ ይሠጣል፡፡ በተጨማሪም የሥራ ክርክር ለማቅረብ የሕብረት ሥምምነት ለመደራደር በማኅበር ስብሰባ ለመገኘት፣ በሴሚናሮችና በስብሰባዎች ለመካፈል እንዲችል ከክፍያ ጋር ፈቃድ ይሰጠዋል፡፡ 
          2. የማኅቡ የኮሚቴ አባሎች በተለያየ ጊዜ ከተለያዩ አቻ ማኅበራት ዕድገት እንዲሁም ለሠራተኞች የሚጠቅም የልምድ ልውውጥና አንዳንድ ግንኙነቶችን በሚያደርጉበት ጊዜ ወይም ለማድረግ ፈልገው ከፋብሪካው እርዳታ በሚጠይቁበት ወቅት ፋብሪካ የፈቃድ ትብብር ያደርጋል፡፡ 
          1. ልዩ ልዩ ተግባሮችን ለማከናወን የሚሰጥ ፈቃድ 
          1. አንድ ሰራተኛ የሥራ ክርክር ለማሣማት ወይም የአሰሪና ሰራተኛ ጉዳይ ሕጎችን ለማስፈፀም ስልጣን ያላቸው አካሎች ዘንድ ጉዳዩን ለማስማት ሲቀርብ ለዚሁ ዓላማ ለጠፋው ጊዜው ብቻ ከክፍያ ጋር ፈቃድ ይሠጠዋል፡፡ 
          2. አንድ ሠራተኛ የሲቪል መብት ሲያስጠብቅ ወይም የሲቪል ግዴታውን ሲፈፅም ለዚሁ ዓላማ ለጠፋው ጊዜ ብቻ ፈቃድ ከክፍያ ጋር ይሠጠዋል፡፡ ከዚህ በላይ የተጠቀሱትን ፈቃዶች ለመውሰድ በቅድሚያ አሠሪውን ማስፈቀድና ማስረጃ ማቅረብ አለበት፡፡ 

          አንቀጽ 30

          የሕዝብ በዓላት

          1. በመንግስት የታወቁ የሕዝብ በዓላት በሙሉ በዓል ናቸው፡፡ የፋብሪካውን የምርት ሂደት ለመጠበቅ ሲባል የሕዝብ በዓላት በሚውሉበት ቀን አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝና በአስተዳደሩም ሲታዘዝ ሰራተኛው የመሥራት ኃላፊነት አለበት፡፡ ክፍያውም በአሰሪና ሰራተኛ ጉዳይ አዋጅ ቁጥር 377/1996 መሠረት ይሆናል፡፡ 

          አንቀጽ 31

          ሕክምና

          1. ድርጅቱ የመጀመሪያ ሕክምና እርዳታ የሚሠጥ ክሊኒክ ያቋቁማል፡፡ 
          2. የድርጅቱ አምቡላንስ ወይም መኪና ይመድባል፡፡ 
          3. በመንግስት የሕክምና ተቋም ለሚወጣ የሕክምና ወጪ 50% (ሃምሣ በመቶ) ይሸፈናል፡፡ 

          አንቀጽ 32

          ለቀብር ሥነ-ሥርዓት የሚደረግ ዕርዳታ

          1. አንድ የፋብሪካው ሠራተኛ ሲሞት ፋብሪካው ቀጥሎ የተዘረዘሩትን ያቀርባል፡፡ 
          1. ፋብሪካው በፋብሪካው ውስጥ ለሚዘጋጅ አስከሬን ሣጥን እና 5 ሜትር የከፈን ጨርቅ ይሠጣል፡፡   
          2. የፋብሪካው ሠራተኛም የሆነ ከዚህ ዓለም በሞት ሲለይ ብር 2000.00 /ሁለት ሺህ ብር/ ማኅበሩ በሚሠጠው ማረጋገጫ መሠረት ለቀብር ማስፈፀሚያ ፋብሪካው ለቤተሰቡ ይሠጣል፡፡ 
          3. በፋብሪካው ሥራ ምክንያት ወይም ለሕክምና ወደ ሌላ ክፍለ ሀገር ሄዶ እዚያው ከዚህ ዓለም በሞት ሲለይ ፋብሪካው የሟች አስከሬን ወደሚኖርበት ክፍለሀገር ወይንም ወደ ሚቀበርበት ያደርሳል፡፡ 
          4. ከዚህ በላይ በተራ ቁጥር 1.1፣ 1.2 የተዘረዘሩትን አገልግሎቶች ለማቅረብ በማይቻልበት ጊዜና የሞት አደጋው የደረሰው ሠራተኛ ከሚሠራበት ከተማ ውጪ ቢሆን ወጪዎን ፋብሪካው ለቀብር ሥነ-ሥርዓት የሚያወጣውን ተመጣጣኝ ገንዘብ ይከፍላል፡፡   
          5. የቀብር ሥነ-ሥርዓቱ በሚፈፀምበት ጊዜ ቁጥራቸው ከሃያ ሰው ያልበለጠ ሠራተኞች ከሥራ ቦታ ወደ ቀብር ቦታ ወደ ሀዘን ከዚያም ወደ ስራ ቦታ የሚያደርስ አንድ ትራንስፖርት መኪና ይመድባል፡፡ 
          6. አንድ ሠራተኛ ከዚህ ዓለም በሞት ሲለይ አስከሬኑ ፋብሪካው ባለው ትራንስፖርት መገልገያ የሚያጓጉዝበት መንገድ ለመኪና አመቺ እስከሆነ ድረስ የቀብር ሥነ-ሥርዓቱ ወደሚፈፀምበት አካባቢ ለማድረስ ይተባበራል፡፡ 

            አንቀጽ 33

            የአደጋ ዋስትና /ኢንሹራንስ/

            1. ከሥራ ጋር ለተያያዘ ጉዳት ወይም ሕመም የሚሠጥ ሕክምና 
            1. በስራ ላይ የሚደርስ አደጋ ወይም ጉዳት ከሥራ ጋር በተያያዘ ሁኔታ ለሚደርስ ሕመም ሁሉ ለኢንሹራንስ ውልና በአሠሪና ሠራተኛ አዋጅ 377/1996 መሠረት ፋብሪካው ይፈፅማል፡፡ 
            2. ሠራተኛው ከመደበኛ ሥራው ላይ ባይሆን እንኳን በኃላፊዎች ትዕዛዝ የፋብሪካው ሥራ በሚያከናውንበት ወቅት ለሚደርስበት አደጋ ፋብሪካው በኢንሹራንስ ውል መሠረት ይፈፅማል፡፡ 
            3. አንድ ሠራተኛ ከሥራ ጋር በተያያዘ አደጋ ወይም ጉዳት ደርሶበት ሆስፒታል ከተኛና ሠራተኛው በሚሠራበት ክፍል የዕድገት ውድድር ቢኖር ሠራተኛው ለውድድር ለመቅረብ የማይችል ሆኖ ከተገኘ የዕድገት ውድድር እስከ ሁለት ወር እንዲዘገይ ይደረጋል፡፡ ሆኖም በዚህ ጊዜ ውስጥ በሥራው ላይ ችግር የሚያስከትል ሁኔታ ካጋጠመ ፋብሪካ ይወስናል፡፡ 
            4. ሠራተኛው በሥራ ላይ እያለ ለሚደርስበት ማንኛውም ሥራ ላይ አደጋ ኢንሹራንስ ዋስትና ይኖረዋል፡፡ 
            5. አንድ ሠራተኛ የሥራ ተግባሩን ፈፅሞ ከወጣ በኋላ ወደ ቤት ለመመለስ ለአንድ ሰዓት ወይም ተግባሩን ለመፈፀም ወደ ሥራው ከመግባቱ በፊት ለአንድ ሠዓት ሥራ ላይ እንዳለ ተቆጥሮ በዚህ ጊዜ ውስጥ ለሚያጋጥመው አደጋ የኢንሹራንስ ዋስትና ይኖረዋል፡፡ ይኸውም ለፋብሪካው ሥራ ጉዳይ ከቤታቸው ተጠርተው ለሚመጡ ሠራተኞችንም ያጠቃልላል፡፡ 
            6. አንድ የፋብሪካው ሠራተኛ በሥራው ምክንያት አደጋ ቢደርስበት ተገቢውን ሕክምና ተደርጎለት እስከመጨረሻው የመዳን ወይም በሥራው ብቁ አለመሆኑን የሐኪሞች ቦርድ ሲያረጋግጥ የሚገባውን ሁሉ ተከፍሎት ከሥራ ይሠናበታል፡፡ 
            7. ሠራተኛው በሥራ ላይ በሚደርስበት አደጋ ወይም ከሥራው ጋር በተያያዘ ሁኔታ ለሚያመው የአካል ጉድለት ክፍያው የኢንሹራንስ ውል መሠረት ይሆናል፡፡ 
            8. ፋብሪካው ከኢንሹራንስ ድርጅት ጋር የሚያደርገው ሥምምነት በየዓመቱ በሚያደርገው የውል እድሣት አንድ ኮፒ ለሠራተኛ ማኅበር በወቅቱ እንዲደርስ ያደርጋል፡፡ 
            9. የሥራ ላይ አደጋ የኢንሹራንስ ዋስትና ያለው ሠራተኛ ሁሉ ከሥራ ወደ ቤት ከቤት ወደ ሥራ ሲሄድ የደረሰበትን አደጋ በ/24/ ሃያ አራት ሰዓት ውስጥ ከፖሊስ ጣቢያ ወይም ለፋብሪካው ክሊኒክ ማስመዝገብና በቂ ማስረጃ ማቅረብ አለበት፡፡ ጉዳት የደረሰበት ሠራተኛ ሪፖርት ለማድረግ ካልቻለ ቤተሰቡ ወይም የአደጋውን ሁኔታ ያየ ማንኛውም ሰው በተወሰነ ሠዓት ውስጥ ለፋብሪካው ማመለክት አለበት፡፡ በተወሰነ ጊዜ ያለተመዘገበ ጉዳት ተቀባይነት የለውም፡፡ 
            10. በሥራ ላይ አደጋ የደረሰበት ሠራተኛ በ24 ሰዓት ውስጥ ለቅርብ ኃላፊው ማሣወቅ አለበት፡፡ የቅርብ ኃላፊውም አስፈላጊውን የአደጋ ቅፅ ሞልቶ ለአስተዳደር ያስተላልፋል፡፡ ሠራተኛውም ለአስፈላጊው ሕክምና ወደ ክሊኒክ ይልካል፡፡ 
            11. ጉዳት የደረሰበት ሠራተኛ ሆን ብሎ በራሱ ላይ ላደረሰው ማንኛውም ጉዳት አሰሪው ኃላፊነት አይኖርበትም፡፡ በተለይም በሚከተሉት ድርጊቶች ምክንያት የሚመጣ ጉዳት ሠራተኛው በራሱ ላይ ሆን ብሎ ያደረሰው ጉዳት እንደሆነ ይቆጠራል፡፡ 

            ሀ/ በአሠሪው አስቀድሞ በግልፅ የተሠጡትን የደህንነት መጠበቂያ መመሪያዎች መጣስ ወይም አደጋ መከላከያ ደንቦችነን መተላለፍ፡፡ 

            ለ/ አካሉን ወይንም አእምሮውን በሚገባ ለመቆጣጠር በማይችልበት ሁኔታ ከመጠጥ ወይንም በአደንዛዥ ዕፅ ሰክሮ በሥራ ላይ በመገኘት፡፡ 

            1. በዚህ ህብረት ሥምምነት ኢንሹራንስ በተመለከተ ያልተጠቀሰ ጉዳይ ቢኖር በአሠሪና ሠራተኛ አዋጅ ቁጥር 377/1996 እና ወደፊትም በሚወጡ ደንቦችና ድንጋጌዎች መሠረት ይፈፀማል፡፡  




            አንቀጽ 34

            ለሠራተኛ የሚሠጥ የገንዘብ ብድር

            1. የገንዘብ ብድር 
            1. ፋብሪካው ለቋሚ ሠራተኞች ችግር የብድር አገልግሎት ይሠጣል፡፡ 
            2. ከአንድ ዓመት በላይ አገልግሎት ያለው የፋብሪካው ሠራተኛ የአንድ ወር ደመወዙን መበደር ይችላል፡፡ ሠራተኛው ለሚበደረው ገንዘብ ከፋብሪካው ሠራተኛ ዋስ ያቀርባል፡፡ ሆኖም የመጨረሻ የፅሁፍ ማስጠንቀቂያ ላይ ያለ ሠራተኛ ብድር አያገኝም፡፡ ዋስ መሆን አይችልም፡፡ 
            3. የፋብሪካው ሠራተኛ በተራ ቁጥር 1.2 የተጠቀሰውን ገንዘብ ከተበደረ፣ የአንድ ወር ደመወዝ የተበደረ በ6 ወር ጊዜ ውስጥ ከፍሎ ይጨርሳል፡፡ የተበደረውን ብድር ሣይጨርስ ተጨማሪ ብድር መጠየቅ አይችሉም፡፡ 
            4. ብድር የሚሠጠው በፋብሪካው ሥራ አስኪያጅ ወይም በሚወክለው ኃላፊ ሲፀደቅ ይሆናል፡፡ 
            5. የተበዳሪና የዋሱ ደመወዝ ተመጣጣኝና ተቀራራቢ መሆን አለበት፡፡ 
            6. አንድ ሠራተኛ ዋስ መሆን የሚችለው ለአንድ ጊዜና ለአንድ ሠራተኛ ብቻ ነው፡፡ 
            7. አንድ ሠራተኛ የተበደረውን ገንዘብ ከፍሎ ሳይጨርስ ሥራውን ቢለቅ ወይም ከዚህ ዓለም በሞት ቢለይ ከጉዳት ካሣው ከሚገባው ሕጋዊ ክፍያ ላይ ቀሪው ዕዳ ተቀናሽ ይሆናል፡፡ ሆኖም ክፍያው ዕዳውን የማይሸፍን ከሆነ ቀሪው ዋሱ ይከፍላል፡፡ 

            አንቀጽ 35

            የትምሕርት ወጪ

            1. በማንኛውም የትምህርት ደረጃ ሠራተኛው በትርፍ ጊዜው የመማር መብት ይኖረዋል፡፡ 
            2. ድርጅቱ ሲፈልግ ሠራተኛውን በሥራ አፈፃፀሙ አወዳድሮ በሀገር ውስጥ ሆነ በውጪ ሀገር ልኮ ወጪውን በመሸፈን ሊያስተምር ይችላል፡፡ 
            3. ሠራተኛ የሚያቀርበው የትምህርት ማስረጃ ከግል ማኅደሩ ጋር ተያይዞ ይቀመጣል፡፡ ውድድር ሲኖር እንደማንኛውም ሠራተኛ ከመወዳደር በቀር ዕድገት ወይንም የደመወዝ ጭማሪ ሊጠይቅበት አይችልም፡፡ 
            4. ፋብሪካው ዝውውር አስፈላጊ ሆኖ ወደ ሌላ ቦታ /ድርጅት/ የሚያዛውረው ሠራተኛ ትምሕርት በመከታተል ላይ ያለ ከሆነ የዓመቱን የትምህርት ፕሮግራም እስከሚፈፅም ድረስ ይጠብቃል፡፡ ሆኖም በሠራተኛው ፈቃድ ከሆነ ዝውውሩ ሊፈፀም ይችላል፡፡ 
            5. አስቀድሞ ለፋብሪካው ላሳወቁና ማስረጃ ለሚያቀርቡ የብሔራዊ ፈተና ተፈታኞች ለፈተናው ቀናት ፈቃድ ከደመወዝ ጋር ይሰጣል፡፡ 

            አንቀጽ 36

            ለሠራተኛው ስለሚሸጡ ምርቶች፣ ስለሚሠጡ ተራፊ ምርት ውጤቶች እና ልዩ ልዩ የተጋቢ ዕቃዎች፡፡

            1. ፋብሪካው ከሚያመርታቸው ምርቶች የተለያዩ ጨርቆች በዓመት አንድ ጊዜ 3 ሙሉ ልብስ እና ሸሚዝ በፋብሪካው የማምረቻ ዋጋ ለእያንዳንዱ ሰራተኛ በመሰረታዊ ሰራተኛ ማህበሩ በኩል መግዛት ይችላል፡፡ 
            2. ለዓመቱ የተፈቀደው ግዢ ለሚቀጥለው ዓመት በፋብሪካው አቅርቦት ምክንያት ካልሆነ በስተቀር አይተላለፍም፡፡ 
            3. የሚሸጡ የተጋቡ እቃዎች ከጨረታ ዋጋ 50% በመቀነስ በመሰረታዊ ሠራተኛ ማህበሩ በኩል ለፋብሪካው ሰራተኞች ይሸጣል፡፡ ማህበሩም ሽያጩን የመከታተልና የማስፈፀም መብት አለው፡፡ 

            አንቀጽ 37 

            ዓመታዊ ጉርሻ 

            1. የዓመት ጉርሻ (ቦነስ) ዋናው ዓላማ የሠራተኛው ምርታማነት ከፍ ለማድረግ እና ለሠራተኛውም በዚሁ ተበረታቶ ምርቱን የበለጠ ለማሳደግ ፋብሪካውን ትርፋማ ለማድረግ እንዲያስችል ነው፡፡ በፋብሪካችን ውስጥ ይህንኑ በግንዛቤ ውስጥ በማስገባት በሚከተለው ሁኔታ ቦነስ ክፍያ እንዲኖር ያደርጋል፡፡ 
            1. ድርጅቱ ትርፍ ካተረፈ የአንድ ወር ደመወዝ ቦነስ ይሰጣል፡፡ ትርፉ ካለፈው ዓመት የበለጠ ከሆነ ደግሞ፣ የአንድ ወር ተኩል ደመወዝ ቦነስ ይሰጣል፡፡ 
            1. ሰራተኛው ለሚቀጥለው በጀት ዓመት የበለጠ ተበረታቶ እንዲሠራ ለማድረግ ጳግሜ 1 ቀን የቦነስ ክፍያው ይከናወናል፡፡ ሒሳቡም በውጪ ኦዲተሮች መመርመር አለበት፡፡ ሆኖም ሒሳቡ ካልደረሰ ከጥቅምት ወር ማለፍ የለበትም፡፡ ክፍያው የሚመለከተው የሙከራ ጊዜውን ጨርሶ አንድ ዓመትና ከዚያ በላይ ላገለገለ ቋሚ ሠራተኛ ሲሀን፣ የተጠቀሰውን የአገልግሎት ዘመን ያሟላ ሠራተኛ በዚህ ተራ ቁጥር ከተጠቀሰው ውጪ በተለያየ መንገዶች፣ በጡረታ፣ በአደጋ፣ በበሽታ፣ በዝውውር፣ በፈቃድ መልቀቅና ሌሎች ፋብሪካውን ቢለቅ፣ 

            ሀ/ ከዓመት በላይ አገልግሎት ስራውን ለሚለቅ ሠራተኛ የቦነስ ክፍያው የሚተመነው የወር ደመወዙ ለ12 ተከፍሎ በአገለገለበት ወር ተባዝቶ ይሆናል፡፡ ያገለገለበት ወር ከግማሽ በላይ በከሆነ እንደ ሙሉ ወር የሚቆጠር ሲሆን ከግማሽ ወር በታች ከሆነ አይቆጠርም፡፡ 

            1. ልዩ ልዩ ፈቃድ ከወሰዱት ሠራተኞች ውስጥ ቦነስ ሚከፍለው ሠራተኛ 

            ሀ/ የዓመት ፈቃድ የወሰዱ 

            ለ/ በሥራ ላይ አደጋ ደርሶበት የሕመም ፈቃድ የተሠጠው 

            ሐ/ የሀዘን ፈቃድ ተሠጥቶት ከሥራ ለሚቀር ሠራተኛ ብቻ ነው፡፡ ከዚህ ውጪ በተለያየ ምክንያቶች ከሥራ ለሚቀር ሠራተኛ ለቀረበት ቀን ቦነስ አይከፈልም፡፡ 

            መ/ ከሥራ ላይ ግንኙነት በሌለው ሕመም ምክንያት ከምድብ ሥራው ላይ ተነስቶ በቀላል ሥራ ላይ የተመደበ ሠራተኛ ቦነስ አይከፈልም፡፡ 

            1. በልዩ ልዩ ምክንያት ከሥራ የወጡ ሠራተኞች ለሠሩበት ጊዜ ጉርሻ/ቦነስ/ ለማግኘት መብት ሲኖራቸው ጉርሻ/ቦነስ/ መክፈል ከተጀመረበት ቀን ጀምሮ እስከ ስድስት ወር ድረስ በአካል መጥተው ካልወሰዱ አይከፈላቸውም፡፡ 
            2. ያለአንዳች ማስጠንቀቂያ ከሥራ በሚያስወጡ ጥፋቶች ፈፅሞ ከሥራ ለተሰናበተ ሠራተኛ የዓመት ጉርሻ /ቦነስ/ አይከፈልም፡፡ 
            3. ከጉርሻ/ቦነስ/ ክፍያ እንዲቀነስ ሠራተኛው ካመለከተ በስተቀር ድርጅቱ የመንግስት ታክስ እንጂ ማናቸውንም ነገር ተቆራጭ አያደርግም፡፡ ሆኖም ጉርሻ ሊከፈለው የሚገባው ሆኖ ከሠራ ለተሠናበተ ሠራተኛ ጉርሻ በሚከፈልበት ጊዜ ማንኛውም ቀሪ ዕዳ ተቀናሽ ይሆናል፡፡ 

            አንቀጽ 38

            ዓመታዊ የደመወዝ ጭማሪ

            1. ድርጅቱ በበጀት ዓመቱ ማትረፉ በውጪ ኦዲተሮች ሲረጋገጥ 15% የደመወዝ ጭማሪ ይሰጣል፡፡ እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር ከሐምሌ 1 ቀን እስከ ሰኔ 30 ቀን ያለውን ቀን ነው፡፡  
            2. የደሞዝ ጭማሪው ከጥቅምት ማለፍ የለበትም፡፡ 
            3. አንድ ሠራተኛ ጭማሪ ለማግኘት ቢያንስ 6/ስድስት/ ወር ፋብሪካውን ማገልገል አለበት፡፡ 



              አንቀጽ 39 

              የአደጋ መከላከያና የሥራ ልብስ 

              1. ሠራተኞች ላይ በሥራ ቦታ አደጋ እንዳይደርስባቸው እንደዚሁም ከሥራቸው ጋር ግንኙነት ባላቸው ሕመሞች ሁሉ ስለ ደህንነታቸው ተገቢውን መከላከያና ጥንቃቄ ማድረግ የፋብሪካው ኃላፊነት ነው፡፡  
              2. ሠራተኛው በስራ ላይ ለሚደርሱ አደጋዎች ጥንቃቄ በሚመለከት የሚሠጠውን መመሪያ ማክበር አለበት፡፡ 
              3. በጥንቃቄ ጉድለት ሳይሆን በስራ ምክንያት የሥራ ልብስ የተቀደደበት ወይም የተበላሸበት ሠራተኛ ለቅርብ ኃላፊው ያመለክታል፡፡ የቅርብ የሥራ ኃላፊውም ሲያምንበት የተቀደደውን ወይም የተበላሸውን መልሶ አዲስ ልብስ ለሠራተኛ እንዲሠጥ ያደርጋል፡፡ 
              4. በሠራተኛ እንዝህላልነት የሥራ ልብስ ቢጠፋበት ወይም ቢሰረቅበት በቂ ማስረጃ አቅርቦ ዋጋውን በሁለት ክፍያ እንዲከፍል ተደርጎ ይሰጠዋል፡፡ 
              5. ሠራተኛው የተሠጠውን የአደጋ መከላከያ የስራ ልብስ በስራ ላይ መጠቀም አለበት፡፡ 
              6. የአደጋ መከላከያ መሣሪያዎችና ሠራተኞችን ጤንነት የሚከታተል የስራ ደህንነት /የሴፍቲ/ ኮሚቴ ይቋቋማል፡፡ 
              7. ሀ/ ፋብሪካው በአባሪ 3 የተመለከቱትን የሠራተኞች የሥራ ልብስ አሰፍቶ ይሠጣል፡፡ 

              ለ/ በዓመት ሁለት ጊዜ የሚሠጡ የስራ ልብሶችንና የአደጋ መከላከያዎችን ምንግዜም በጥር ወር የመጀመሪያው ዓመት ሲሰጥ የሁለተኛው መንፈቅ ወይም ግማሽ በሐምሌ ወር ይሰጣል፡፡  

              1. ለጥበቃ ሠራተኞች የሚሠጠው ካፖርትና የዝናብ ልብስ በሁለት ዓመት አንድ ጊዜ ነው፡፡ ከሌሎቹም አባሪ 3 የተጠቀሱት የዝናብ ልብስ በዚሁ መሠረት ይሆናል፡፡ 
              2. በአባሪ 3 የተፈቀደው ሣሙና የሚሠጠው በወር በቁጥር 3(ሦስት) ሣሙና ነው፡፡ 
              3. የላስቲክ፣ የቆዳና የሸራ ጓንት፣ ጎግል ማስክ፣ መነፅር አገልግሎታቸው እንዳበቃ ወይንም ከጥቅም ውጪ መሆናቸው ሲረጋገጥ ብቻ ይሠጣል፡፡ 
              4. የስራ ልብስና ጫማ በዓመት ሁለት ጊዜ በየስድስት ወሩ ይሰጣል፡፡ 
              5. በአባሪ 3 ስህተት ሲያጋጥም በኢንስፔክተር ጥናት መሠረት ይፈፀማል፡፡  




              አንቀጽ 40

              የሥነ-ሥርዓት እርምጃዎች

              የሥነ-ሥርዓት /ዲሲፕሊን/ እርምጃዎችና የቅሬታ 

              አቀራረብ ሥነ-ሥርዓት

              1. የቅጣት እርምጃ አወሳሰድ 
              1. የፋብሪካው የሥራ እንቅስቃሴ ሊጎለብት የሚችለው ሠራተኛው ያለውን ጉልበትና ዕውቀት ሳይቆጥብ በምርት ሥራ ላይ አውሎ ምርታማነቱን ሲያሳድግ ላብ አደራዊ ሥነ-ምግባር ሲጠናከር በመሆኑ፣ 
              2. ይህንንም ዓላማውን ከግብ ለማድረስ በሚያደርገው ጥረት መላው ሠራተኛ ተሳታፊ እንዲሆን ለማነቃቃትና ዓላማውን ለማስመስከር ሲባል በእጥፊው ላይ የሥነ-ሥርዓት እርምጃ መውሰድ የግድ አስፈላጊ በመሆኑ ምክንያት በዚህ ክፍል የተመለከተው የሥነ-ሥርዓት እርምጃዎች ተግባራዊ ይሆናል፡፡ 
              1. ከቅጣት በፊት የሚወሰዱ የሥነ-ሥርዓት እርምጃዎች፡፡ 
              1. ማንኛውም ሠራተኛ ጥፋት መፈፀሙን የቅርብ አለቃው እንደተረዳ በአጥፊው ሠራተኛ ላይ ተገቢውን የሥነ-ሥርዓት እርምጃ በዚህ ሕብረት ሥምምነት መሠረት ይወስዳል፡፡ ሆኖም ከሥራ የሚያሳግዱና የሚያስወጡ ጥፋቶች ሆነው ሲገኙ የክፍል ኃላፊው ከበቂ ማስረጃ ጋር ለአስተዳደሩ ያቀርባል፡፡ አስተዳደሩም ካረጋገጠ በኋላ በዚህ ህብረት ሥምምነትና በአሠሪና ሠራተኛ አዋጅ 377/1996 መሠረት የሥነ-ሥርዓት እርምጃ ይወስዳል፡፡  
              2. በየደረጃው ክፍል የሚወሰዷቸው የሥነ-ሥርዓት እርምጃዎች በግልባጭ ለአስተዳደሩ ያሳውቃል፡፡ 
              1. ላደረሰው ጥፋት ተጠያቂ በመሆን ያለአንዳች ማስጠንቀቂያ ከስራ የሚያስወጡ ጥፋቶች፡፡ 
              1. የተከለከለ ቦታ ሲጋራ በማጨስ ጉዳት ያደረሰ፣ 
              2. የፋብሪካውን ንብረት ያለፈቃድ ለግል ጥቅም ያዋለ ወይም ለሌላ ሰው የሠጠ ወይም እንዲወስዱ ያደረገ ወይም የረዳ፣ 
              3. ሆን ብሎ በእሳት ወይንም በኤሌክትሪክ በፋብሪካዉ ንብረት ላይ ጉዳት እንዲፈጠር ያደረገ ወይም ያበረታታ፣ 
              4. በወር ውስጥ መደዳውን ያለፈቃድ አምስት /5/ የሥራ ቀን የቀረ ወይም በአንድ ዓመት ውስጥ በጠቅላላው ለ30 የሥራ ቀን ያለበቂ ምክንያት ከሥራ መቅረት፣ 
              5. ሀሰት መሆኑን እያወቀ ሊያገኝ የማይገባውን ጥቅም ለማግኘት ወይም ለሌሎች እንዲያገኙ ለማድረግ የተሠጠውን ፈቃድ ሰርዞ /ደልዞ/ ወይም ከተፈቀደለት በላይ የጨመረ ወይም የባለስልጣን ፊርማ አስመስሎ የፈረመ እንዲሁም የደለዘ ወይም ሀሰተኛ ሰነድና ሀሰተኛ የአደጋ ሪፖርት ያቀረበ፣ ፕሮዳክሽን በትክክል ያልመዘገበ ምርት መቆጣጠሪያ መሣሪያዎችን የጎረጎረ ወይንም ያበላሸ በጠቅላላው የፋብሪካው መዛግብት እንዲቃወሱ ያደረገ፡፡ 
              6. ትክክለኛ ያልሆነ ማስረጃ ወይም ሠርተፍኬት ያቀረበ ወይም የሌላውን ሠው የምስክር ወረቀትና የሥራ ልምድ ማስረጃ የተጠቀመና ስሙን ሰው የተቀጠረ፣ 
              7. የፋብሪካውን ተሽከርካሪ ያለፈቃ የነዳ ወይም ለግል ጥቅሙ ያዋለ ለሌላ ሰው ጥቅም ያዋለ ወይም ሌላ ሰው እንዲነዳ ያደረገ፣ 
              8. በስራ ላይ ሰክሮ የተገኘ 
              9. ለፋብሪካው ተሽከርካሪ የተፈቀደውን ነዳጅ ወይም ዘይት ለራሱ ጥቅም ወይም ለሌላ ያዋለ፣ 
              10. አደጋ መፈጠሩን ወይም ብልሽት መድረሱን እያወቀ ያልገለፀ ወይም በሚያሽከረክረው መኪና ላይ የደረሰውን ጉዳት የደበቀ ወይም የተረከበውን መኪና፣ መፍቻቸውን፣ ጎማዎች፣ ክሪኮችና የመሳሰሉትን ጥሎ የደበቀ፡፡  
              11. በፋብሪካው ውስጥ በሠዓት ቁጥጥር፣ በምርት ሚዛኖች በጨርቅ መለካት፣ በትርፍ ሠዓት አሞላል በደመወዝ ልኬት በኮንትራት ወይም በቀን ሠራተኞች አቀጣጠርና አከፋፈል ስራ ላይ ተመድቦ የሚሰራ ማንኛውም ሠራተኛ ከትክክለኛ አሰራር ውጪ ሰርቶ ሌላውን ሠራተኛ ሆን ብሎ የጠቀመ ወይም የጎዳ፣ 
              12. ኃላፊነቱን የሚያስት ጉቦ ወይም መደለያ የሠጠ ወይም የተቀበለ እንዲሠጥ ወይም እንዲቀበል ያደረገ፣ 
              13. በማንኛቸውም የፋብሪካው መሣሪያ ወይም ንብረት ላይ ሆን ብሎ ከባድ ብልሽት ያደረሰ፣ 
              14. በዘብ አጠባበቅ ጉድለት በፋብሪካው ወይም በፋብሪካው ንብረት ወይም በሠራተኛው ላይ ጉዳት እንዲደርስ ያደረገ ወይም የረዳ፣ 
              15. በሥራ ቦታና ጊዜ በፋብሪካው ውስጥ ወይም ፋብሪካው በመደበው ትራንስፖት አገልግሎት ላይ የተደባደበ የበላዮቹን ወይም የበታቾቹን የሚመታ፣ 
              16. በዚህ ሕብረት ሥምምነት የተመለከተው የመጨረሻ ማስጠንቀቂያ ከተቀበለ በኋላ ጥፋት የፈፀመ፣ 
              17. በፋብሪካ ውስጥ የዝሙት ተግባር የፈፀመ፣ 
              18. ያለ ኃላፊው ፈቃድ ሠነድ ያወጣ ወይም ሚስጥር ያባከነ ማንኛውም ሠራተኛ በማስረጃ ሲረጋገጥ፡፡ 

              አንቀፅ 41

              የቅጣት ማሻሻያ ምክንያቶች

              1. የፋብሪካ ሥራ አስኪያጅ ወይም አስተዳደር መመሪያ ኃላፊ ወይም በግልፅ የተወከለው ባለ ሥልጣን አጥጋቢና በቂ የሆነ ምክንያት መሆኑን በትክክል ከተረዳ በአንድ ሠራተኛ ላይ የተወሰደው የሥነ-ሥርዓት እርምጃ ለማሻሻል ይችላል፡፡ 
              2. አንድ ሠራተኛ ሚያስቀጣ አንድ ጥፋት ፈፅሞ እርምጃ ከተወሰደ በኋላ ለተከታታይ ስድስት ወር ጊዜ ጥፋት ሳይፈፅም ሁኔታዎችን አሻሽሎ ከተገኘ የተወሰደበት የሥነ-ሥርዓት እርምጃ እንዳልተወሰደበት ተቆጥሮ የነበረው መልካም ስሙ ይታደስለታል፡፡ 
              3. በተለይ ጥፋቶች ከሥራ ስለሚወጡ ሠራተኞች፡፡ 
              1. ፋብሪካው የደረጃ ዕድገትና የደመወዝ ጭማሪ በሚያደርግበት ጊዜ ሠራተኛው ለሚያጠፋቸው ጥፋቶች የተያዙትን ማስረጃዎች እስከ ተከታታይ ስድስት ወር /6/ ወር ጊዜ ሊጠቀምባቸው ይችላል፡፡ 
              2. ፋብሪካው የመጨረሻ የፅሁፍ ማስጠንቀቂያ የሠጠውን ሠራተኛ ለማኅበሩ በፅሁፍ ያሳውቃል፡፡ 
              3. አንድ ሠራተኛ በቀሪነት ምክንያት ደመወዙ ከመቀነሱ በፊት ማስረጃውን ማቅረብ ይኖርበታል፡፡ 

              አንቀጽ 42

              የቅሬታ አቀራረብ ሥነ-ሥርዓት

              1. አንድ ሠራተኛ ከስራ ጋር በተያያዘ ጉዳይና በተወሰደበት የሥነ-ሥርዓት እርምጃ ቅሬታ ሲሰማው ውሳኔው ከደረሰው ቀን አንስቶ በ3 ቀን ውስጥ ለምርት ክፍል ሥራ አስኪያጅ ቅሬታውን በፅሁፍ ያቀርባል፡፡ የምርት ክፍል ሥራ አስኪያጅም ከአቅም በላይ የሆነ ምክንያት ካላጋጠመው በስተቀር በሦስት ቀን ውስጥ ጉዳዩን መርምሮ ውሳኔ ይሠጣል፡፡ 
              2. የምርት ክፍል ሥራ አስኪያጅ በሠጠው ውሳኔ ያረካ ከሆ በማኅበሩ ተወካይ በኩል ወይም በግሉ በሁለት ቀን ውስጥ ለአስተዳደርና ፋይናንስ ኃላፊ ያቀርባል፡፡ የአስተዳደርና ፋይናንስ ክፍሉም የተወሰደውን እርምጃ አገናዝቦ በአራት ቀን ውስጥ ውሳኔ ይሠጣል፡፡ 
              3. ማኅበሩ በአስተዳደርና ፋይናንስ ውሳኔ የማይረካ ከሆነ በአስራ አምስት ቀናት ውስጥ ክሱን ለሚመለከተው ሕጋዊ አካል የማቅረብ ወይም ባለጉዳዩን እንዲያቀርብ ሊያደርግ ይችላል፡፡ 
              4. ማንኛውም ቅሬታ ከዚህ በላይ የተዘረዘረውን ደረጃ ጠብቆ በተወሰነው ጊዜ ካልቀረበ በስተቀር ተቀባይነት የለውም፡፡


              አንቀጽ 43

              በወንጀል ለሚታሠሩ ሠራተኞች

              1. በሠራተኛው ላይ ከ30 ቀናት ለማይበልጥ ጊዜ የእስራት ፍርድ ተወስኖበት ከስራ ሲቀር እና ሕጋዊ ማስረጃ ሲያቀርብ እንደ ሁኔታው አይቶ ወደ ሥራው ሊመልሰው ይችላል፡፡ 
              2. የፋብሪካው ሠራተኛ ታስሮ በነፃ ሲለቀቅና በተራ ቁጥር 1 መሰረት ወደ ስራው የመመለስ ዕድል ካላገኘ በሕጉ መሠረት ሊከፈለው የሚገባው ክፍያ ካለው ይከፈለዋል፡፡
              3. በተራ ቁጥር 1 የተጠቀሰው በዚህ ሕብረት ሥምምነት ውስጥ ያለአንዳች ማስጠንቀቂያ ከሚያስወጡ ጥፋቶች ጋር በተያያዘ ጉዳይ ከሆነ ተፈፃሚነት አይኖረውም፡፡ 

              አንቀጽ 45

              ጠቅላላ ሥምምነቶችና ውሳኔዎች በዚህ ሕብረት ሥምምነቶች ያልተጠቀሱ ጥፋቶች

              በዚህ ሕብረት ሥምምነት ያልተጠቀሱ ጥፋቶች ቢከሰቱ ፋብሪካውንና ሠራተኛ ማኅበሩ በጋራ ተነጋግረው በዚህ ሕብረት ሥምምነት ውስጥ ከተዘረዘሩ ጥፋቶች ጋር በማገናዘብ ወይም በአሠሪና ሠራተኛ አዋጅ 377/1996 መሠረት እርምጃ ለመውሰድ ይቻላል፡፡ 

              አንቀጽ 46

              ወደፊት ስለሚወጡ ሕጎች ወይም ሥምምነቶች

              1. በዚህ ሕብረት ሥምምነቶች ያለተካተቱ ድንገተኛና ጊዜ ማይሠጡ ጉዳዮች ሲያጋጥሙ ፋብሪካውና የሰራተኛ ማኅበሩ በሚያደርጉት ሥምምነት በሕብረት ሥምምነት ውስጥ እንዲካተቱ ይደረጋል፣ ይህን በሠራተኞች ማሕበራዊ ጉዳይ መ/ረት ከተመዘገበ በኃላ ተፈፃሚ ይሆናል፡፡ 
              2. በአዋጅ 377/1996 እንደተመለከተውና ወደፊት በሚወጡ ሕጎች፣ ደንቦችና መመሪያዎች ለሠራተኛው ይበልጥ የሚጠቅሙ ሆኖ ከተገኙ በሥራ ላይ ለማዋል ይህ የሕብረት ሥምምነት አያግደውም፡፡ 
              3. ሠራተኛው በዚህ ሕብረት ሥምምነት መሠረት ሊያገኝ የሚገባውን ጥቅም ወይም መብት ፋብሪካው ሊቀንስበት አይችልም፡፡

              አንቀጽ 47

              የሀብት ሥምምነት ፀንቶ የሚቆይበት ጊዜ

              1. በማኅበር ኢንዱስትሪ ኃ/የተ/የግ/ማኅበር ፋብሪካና በሠራተኛ ማኅበሩ መካከል፣ ተፈርሞ በሠራተኛ ማኅበራዊ ጉዳይ መ/ቤት ፀድቆ ከተመዘገበ ከመጀመሪያው ቀን አንስቶ ለ 3 /ሦስት/ ዓመት የፀና ይሆናል፡፡ 
              2. ይህ የሕብረት ሥምምነት ከዛሬ_____________ቀን 2008ዓ.ም ጀምሮ የፀና ይሆናል፡፡ 


              የተስማሚ ወገኖች ፊርማ


              ስለድርጅት  ስለሠራተኛ ማኅበሩ 

              ሥም፡  ________ ሥም፡  ________

              ፊርማ፡ ________ ፊርማ፡ ________

              ቀን፡ ________ ቀን፡ ________


              ተደራዳሪዎች

              ስለድርጅቱ  ስለሠራተኛ ማኅበሩ 

              1. አቶ ተስፋዬ አማረ  1. አቶ መሃመድ ናስር
              2. አቶ አበራ አንጃ  2. አቶ ደረጀ ለታ 








              ETH Mahaver Industry P.L.C -

              Start date: → Not specified
              End date: → Not specified
              Name industry: → Manufacturing
              Name industry: → Manufacture of textiles
              Public/private sector: → In the private sector
              Concluded by:
              Name company: →  Mahaver Industry P.L.C
              Names trade unions: →  የማሀቪር ኢንዱስትሪ ኃ/የተ/የግል ማኅበርመሠረታዊ የሠራተኛ መኅበር

              TRAINING

              Training programmes: → Yes
              Apprenticeships: → No
              Employer contributes to training fund for employees: → No

              SICKNESS AND DISABILITY

              Provisions regarding return to work after long-term illness, e.g. cancer treatment: → No
              Paid menstruation leave: → No
              Pay in case of disability due to work accident: → Yes

              HEALTH AND SAFETY AND MEDICAL ASSISTANCE

              Medical assistance agreed: → Yes
              Medical assistance for relatives agreed: → No
              Contribution to health insurance agreed: → Yes
              Health insurance for relatives agreed: → No
              Health and safety policy agreed: → Yes
              Health and safety training agreed: → No
              Protective clothing provided: → Yes
              Regular or yearly medical checkup or visits provided by the employer: → No
              Monitoring of musculoskeletal solicitation of workstations, professional risks and/or relationship between work and health: → 
              Funeral assistance: → Yes
              Minimum company contribution to funeral/burial expenses: → ETB 

              WORK AND FAMILY ARRANGEMENTS

              Maternity paid leave: → 13 weeks
              Maternity paid leave restricted to 100 % of basic wage
              Job security after maternity leave: → No
              Prohibition of discrimination related to maternity: → No
              Prohibition to oblige pregnant or breastfeeding workers to perform dangerous or unhealthy work: → 
              Workplace risk assessment on the safety and health of pregnant or nursing women: → 
              Availability of alternatives to dangerous or unhealthy work for pregnant or breastfeeding workers: → 
              Time off for prenatal medical examinations: → 
              Prohibition of screening for pregnancy before regularising non-standard workers: → 
              Prohibition of screening for pregnancy before promotion: → 
              Facilities for nursing mothers: → No
              Employer-provided childcare facilities: → No
              Employer-subsidized childcare facilities: → No
              Monetary tuition/subsidy for children's education: → No
              Leave duration in days in case of death of a relative: → 3 days

              GENDER EQUALITY ISSUES

              Equal pay for work of equal value: → No
              Discrimination at work clauses: → Yes
              Equal opportunities for promotion for women: → No
              Equal opportunities for training and retraining for women: → No
              Gender equality trade union officer at the workplace: → No
              Clauses on sexual harassment at work: → No
              Clauses on violence at work: → No
              Special leave for workers subjected to domestic or intimate partner violence: → No
              Support for women workers with disabilities: → No
              Gender equality monitoring: → No

              EMPLOYMENT CONTRACTS

              Trial period duration: → 45 days
              Part-time workers excluded from any provision: → No
              Provisions about temporary workers: → No
              Apprentices excluded from any provision: → No
              Minijobs/student jobs excluded from any provision: → No

              WORKING HOURS, SCHEDULES AND HOLIDAYS

              Working days per week: → 6.0
              Maximum overtime hours: → 12.0
              Paid annual leave: → 14.0 days
              Paid annual leave: → 2.0 weeks
              Rest period of at least one day per week agreed: → Yes
              Paid leave for trade union activities: →  days
              Paid leave to attend court or for administrative duties: →  days
              Provisions on flexible work arrangements: → No

              WAGES

              Wages determined by means of pay scales: → 
              Adjustment for rising costs of living: → 

              Wage increase

              Wage increase: →  %

              Once only extra payment

              Once only extra payment due to company performance: → Yes

              Premium for overtime work

              Allowance for commuting work

              Meal vouchers

              Meal vouchers provided: → Yes
              Meal allowances provided: → No
              Free legal assistance: → No
              Loading...